Monday, July 11, 2016

ዜጎችን ማፈናቀል መግደልና ማሰደድ የህወሃት አይነተኛ መግለጫዎች ናቸው

ህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ወደ ስልጣን ከመጣበት ጊዜ አንስቶ በአገራችንና በህዝባችን ላይ ሲፈጽም የቆየውና እየፈጸመ ያለው ግፍና ስቃይ ተዘርዝሮ የሚያልቅ አይደልም። አፈና፣ እስር፣ ግድያና ዜጎችን ማፈናቀል አይነተኛ መግለጫዎቹ የሆነው ይህ የህወሃት አገዛዝ፣ ሰፋፊ የእርሻ መሬቶችንና የከተማ ቦታዎችን በመቸብቸብ ሃብት ለማካበት ባለው ዕቅድ በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን እትብታቸው ከተቀበረበት ቀዬና የትውልድ መንደሮቻቸው በግፍ እንዲፈናቀሉ አድርጎአል። አሁንም እያደረገ ነው። ሰሞኑን በአዲስ አበባ በንፋስ ስልክ ክፍለ ከተማ ቀርሳና ኮንቶማ በተባሉ ቀበሌዎች ከ30 ሺ በላይ የሚገመት ህዝብ ለአመታት ከኖረበት መኖሪያ ቤቶች በሃይል ተገፍትረው በመውጣት ጎዳና ላይ እንዲበተኑ ተደርጎአል። በዚህም እርምጃ ምክንያት አቅመደካማ የሆኑ አዛውንቶች፤ ነፍሰጡሮችና ከወለዱ ገና ሳምንታት ያልሞላቸው እመጫቶች፤ የሚያጠቡ እናቶች፤ ህጻናትና ለጋ ወጣቶች ለከፋ ችግር ተዳርገው ለቅሶና ዋይታ በማሰማት ላይ ናቸው። በስንት ልፋትና ድካም ከሰሩዋቸው ቤቶች ተለዋጭ ቦታ ሳይሰጠን ወይም ካሳ ሳይከፈለን አንወጣም በማለት ለማንገራገር የሞከሩ 10 ሰዎች በፖሊስ ጥይት ተገደለዋል፤ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ደግሞ ለእስር ተዳርገዋል። ህወሃት እንዲህ አይነት የጭካኔ እርምጃ እየወሰደ ያለው በክፍለ ከተማው የሰፈሩት ሰዎች “ህገወጦች ናቸው” በሚል ሰበብ ነው። ትናንት ባዶ እግራቸውን ነፍጥ አንግበው ቤተመንግሥቱን የተቆጣጠሩና ጄሌዎቻቸው ከመሃል ከተማው ዜጎችን እያፈናቀሉ ቪላና ሰማይ ጠቀስ ፎቆች ሲገነቡ ህገወጥ ያልተባሉት ሰዎች፣ አረብ አገር ድረስ ተጉዘው በግርድና ሥራ ሳይቀር በመሥራት ባገኙት ገንዘብ በአገራቸው መሬት ላይ ጎጆ የቀለሱ ለምንድነው ህገወጥ የሚባሉት የሚለውን ለታሪክ ፍርድ እንተወውና እነዚህ ህገወጥ የተባሉ ሰዎች በመንግሥት ይዞታ ሥር ካሉ የአገልግሎት ድርጅቶች ጋር ተዋውለው መብራትና ውሃ አስገብተው ሲጠቀሙ መኖራቸው፤ ገንዘብ በማዋጣት መንገድ፤ ጤና ጣቢያዎችንና ትምህርት ቤቶችን በከተማው አስተዳደር ድጋፍ ማስገነባታቸው፤ የህወሃት የንግድ ድርጅቶች በሚሊዮኖች የሚቆጠር ትርፍ ለሚዝቁበት የአባይ ግድብ ቦንድ በየመኖሪያቤታቸው ቁጥር ሲሸጥላቸው የነበረና የምዕራቡን አለም ለማደናገር በየአምስት አመቱ የሚደረገውን የምርጫ ድራማ ለማድመቅ በግዳጅ እንዲመዘገቡና ድምጽ እንዲሰጡ ሲደረጉ መቆየታቸው ብቻውን አገዛዙ ሲመቸው እውቅና ሰጪ ሳይመቸው ደግሞ እውቅና ነሺ መሆኑን የሚያሳይ፣ ለፍትህና ለርእትዕ የማይሰራ የዘራፊዎች ቡድን በመሆኑ፣ የድሆችን ቤቶች ለማፍረስ የወሰደው እርምጃ በየትኛውም መስፈረት ተቀባይነት የሌለው ህገወጥ ድርጊት ነው። ለነገሩ ህገወጥ ከሆነ ቡድን ህጋዊነትን መጠበቅ አይቻልምና ወያኔ በህግ ሽፋን የሚወስዳቸው እርምጃዎች ሁሉ ህገወጥነታቸውን አይለውጠውም።
አባቶቻችን አገራቸውን ከባዕድ ወረራ ለመከላከል ደማቸውን ያፈሰሱትና አጥንታቸውን የከሰከሱ መጪው ትውልድ በአገሪቱ አንገት ማስገቢያ ጎጆ እንዲኖረው በማሰብ እንጅ፣ በደምና በአጥንት የተገዛው መሬት ለውጭ አገር ዜጎች እንዲቸበቸብ ወይም በመንግስት ስም የተደራጁ ሽፍቶች እንዲዘርፉት አልነበረም።
ሌላው አስገራሚና አሳዛኙ ነገር እንዲህ አይነት ሰቆቃ የተፈጸመባቸውና በዚህ ክረምት ወቅት ቤቶቻቸው ፈርሶና ንብረቶቻቸው ወድሞ ወደ ፍጹም ድህነት እንዲገቡ በተደረጉት ዜጎች መሬት ላይ፣ ህወሃት ኮንዶሚኒዬሞችን ገንብቶ ለዲያስፖራ ለመቸብቸብ ዕቅድ ያለው መሆኑ ነው። ዲያስፖራው አገዛዙ በወገኖቹ ላይ የሚፈጽማቸውን ሰቆቃና ግድያ በማጋለጥ ሥራ ላይ በመጠመዱ የህወሃት መሪዎች እረፍት አጥተዋል። በተለይ ከምርጫ 97 ወዲህ አጋዚ የተባለው ሃይል በሰብአዊነት ላይ የሚፈጸም ወንጀል የቀን ጉዳይ ካልሆነ በቀር በአለም አቀፍ ወንጀል እንደሚያስጠይቅ ወያኔ ይረዳል። ይህንን ስጋት ለማስቆም የዲያስፖራን እንቅስቃሴ ማዳከም እንደስትራቴጂ ነድፎ መንቀሳቀስ የጀመረው የነ ቴዎድሮስ አድሃኖም አገዛዝ፣ ዲያስፖራውን በጥቅም በመከፋፈል ስጋቱ ይቀነሳል ብሎ ያምናል። ከዚህም በተጨማሪ አገር ውስጥ የሚደረገውን አልገዛም ባይነት ትግል ለማጠናከር የዲያስፖራው እምቅ ሃይል የሚፈጥረውን ተአምር ህወሃት አውቆታል። ላፍቶ ክፈለ ከተማ 40 በ 60 በተባለው ፕሮጄክት የኮንዶሚኒዬም ባለቤት በመሆን የአገራቸውንና የወገኖቻቸውን ስቃይ ለማራዘም ላኮበኮቡ የዲያስፖራ አባላት እየተመቻቸች ያለ ሰፈር ነው። ከውስጧ እየተሰማ ያለው ለቅሶና ዋይታ የማይቆረቁራቸው ፤ ኮንዶሚኒዬም ቤት የሚያማልላቸው ዲያስፖራዎች አይኖሩም አይባልም።
አርበኞች ግንቦት 7 የህወሃት አገዛዝ ዜጎችን በመግደልና በማሰር ከቀያቸውና ከመኖሪያቤታቸው በሚያፈናቅለው የከተማም ሆነ የገጠር መሬት ላይ ማንም ሰው በህግ ፊት በዘላቂነት የሚጸና መብት ሊያገኝ ይችላል ብሎ አያምንም። ህወሃት በሚወረውርላቸው የጥቅም ፍርፋሪ የወጎኖቻቸውን ስቃይና መከራ ዕድሜ እያራዘሙ ያሉ ከየማህበረሰቡ የተገዙ ስላሉ በተለመደው ርካሽ ዋጋ በንጽጽር ደህና መኖር እየቻለ ካለው የዲያስፖራ ማህበረሰብ ሰዎችን መሸመት እችላለሁ ብሎ ህወሃት እየተንቀሳቀሰ ነው። በቴዎድሮስ አድሃኖም ጽ/ቤት ተዘጋጅቶ በተግባር እንዲተረጎም በውጪ አገር ባሉ የወያኔ ኤምባሲ ሁሉ የተበተነው የዲያስፖራ ፖሊሲ አላማ ይሄ ነው። ቀርሳና ኮንቶማ በእንዲህ አይነት ርካሽ ጥቅም የሚሸመቱ የዲያስፖራ አባላትን ለማሰባሰብ እየተዘጋጀ ያለ ሰፈር ነው። አርበኞች ግንቦት 7 የሶስት ቀን አራስ በተገደለችበት፤ በርካታ እናቶች፤ አቅመደካማ አዛውንቶችና ታዳጊ ህጻናት ተፈናቅለው ለጎዳና ተዳዳሪነት በተዳረጉበት ቦታ ላይ የሚገነባውን ኮንዶሚኒዬም፤ ለተለያዩ አገልግሎት የሚሆኑ ህንጻዎች ወይም ሌላ ኢንቬስትመንት ባለቤት ለመሆን በየዋህነት ያሰፈሰፉ ካሉ ውሳኔያቸውን ቆም ብለው እንዲያጠኑት ይመክራል። ከቤታቸው ተፈናቅለው እንባቸውን እያፈሰሱና በየሜዳው ተበትነው የሚንከራተቱ ወገኖቻችን እንባ ሳይደርቅ ህወሃት ወደ መጨረሻው ከርሰመቃብር ይወርዳል። ይህ ምኞት ሳይሆን የቆምንለትና እየሞትንለት ያለው ትግል ውጤት ነው።
ወያኔ ሃብት ለማካበት በሚያጧጡፈው የመሬት ንግድ የሚፈናቀሉ ወገኖቻችን ህይወት ሁላችንንም ይመለከታል። የአገሪቱን ዜጎች ለጎዳና ተዳዳሪነት በመዳረግ የሚገነቡ አዳዲስ ህንጻዎችና መንገዶች ልማት ሳይሆን ማህበራዊ ቀውስ በመፍጠር ህብረተሰቡን ለከፍተኛ ችግር የሚዳርግ አደጋውም ለአገር የሚተርፍ ነው። አልጠግብ ባይ ጥቂት የህወሃት አመራሮች ህዝባችንን ሲያፈናቅሉትና አገር አልባ ሲያደርጉ ዝም ብሎ መመልከት ችግሩ እንዲባባስና እያንዳንዳችን የጥቃቱ ሰለባ እንዲንሆን መጋበዝ ነው። አርበኞች ግንቦት 7 ይህንን የህወሃት ዜጎችን የማፈናቀል እርምጃ ለማስቆምና በግፍ ለተገደሉ ወገኖቻችን በህግ ለመፋረድ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በያለበት ጸረ ወያኔ ትግሉን እንዲያፏፉምና ትግሉን እንዲቀላቀል ወገናዊ ጥሪውን ያቀርባል።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!

Monday, May 23, 2016

ዛሬ በመርካቶ አሜሪካን ጊቢ አካባቢ የበርካታ ድሆች ቤት እየፈረሰ ነው


(ዘ-ሐበሻ) ካለምንም በቂ ካሳና ካለምንም የሕዝብ ይሁንታ በመርካቶ አካባቢ በተለምዶው አሜሪካን ጊቢ አካባቢ በርካታ የድሆች መኖሪያ ቤቶች  እና የንግድ ቤቶች በልማት ሰበብ ዛሬ እንደፈረሱ ከስፍራው የደረሱን መረጃዎች አመለከቱ::
እነዚህ ቁጥራቸው በርካታ የሆኑ መኖሪያ ቤቶች ውስጥ ለረዥም ዓመታት የኖሩት ወገኖች የሚኖሩበት ቤት ለሃብታሞች በሚሊዮኖች ብር ስር ዓቱ እየቸበቸበው ሲሆን ለነዋሪዎቹ በቂ የሆነ ካሳ አለመከፈሉ ብዙዎችን እያስቆጣ ነው::
ዛሬ ከፈረሱት መኖሪያ ቤቶች በተቸማሪ የተለያዩ የንግድ ድርጅቶችም እንደፈረሱ ያስታወቁት ምንጮች ሕዝቡ መሬቱ ለሃብታሞች ሲሰጥበት በቁጭት እየተምከነከነ መሆኑን አስረድተዋል::

Monday, May 9, 2016

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ያልተወራረደና የተበላሸ ብድሩ ከ12 ቢሊዮን ብር በላይ ደርሷል።

ሚያዚያ ፩(ግንቦት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በየአመቱ በሚያወጣቸው የሂሳብ አያያዝ መግለጫዎቹ ከፍተኛ ትርፍ እንዳገኘ ሲናገር የቆዬው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ2006 እና 2007 ዓም ባሉት 2 ዓመታት ብቻ 11 ቢሊዮን 273 ሚሊዮን ብር ያላወራረደው ገንዘብ ሲኖር፣ 1 ቢሊዮን 300 ሚሊዮን ብር ደግሞ የተበለሻ ብድር እንዳለው ሰነዶች አመለከቱ።
በአውሮፓውያን አቆጣጠር እስከ ሰኔ 30፣ 2014 ድረስ የተለያዩ የድርጅቱ ቅርንጫፍ ባንኮች 3 ቢሊዮን 590 ሚሊዮን ከ30 ሳንቲም ፣ በ2013 ደግሞ 6 ቢሊዮን 956 ሚሊዮን ከ20 ሳንቲም ያላወራረዱት ገንዘብ መኖሩን ከንግድ ባንኩ ሰራተኞች የተገኘው የሂሳብ መዝገብ ያሳያል።
ብድር ወስደው መክፈል ያልቻሉት ድርጅቶችና ብድራቸው በተበላሸ ብድር መዝገብ ከሰፈሩት መካከል፣ ሳይጀን ዲማ ቴክስታይል ፋብሪካ 437 ሚሊዮን ብር፣ ሙሉነህ ካካ ላኪ ድርጅት 94.2 ሚሊዮን ብር፣ አኪር ግንባታ 87.1 ሚሊዮን ብር፣ ካራቱሬ እርሻ ደርጅት 55.3 ሚሊዮን ብር፣ ባዘን እርሻ እና ኢንዱስትሪ ልማት የግል ማህበር 42.1 ሚሊዮን ብር፣ የጌታ ትሬዲንግ 39.3 ሚሊዮን ብር፣ ማሜ ብረታብረት ፋብሪካ 39.2 ሚሊዮን ብር፣ የገነት ላኪና 62 ሚሊዮን ብር፣ ሸበሌ ትራነስፖርት 17.2 ሚሊዮን ብር፣ ፍጹም ዘአብ አስገዶም 14.2 ሚሊዮን ብር ቤድፋም ኢንተርናሽናል 21 ሚሊዮን ብር ይገኙበታል።
ባንኩ በ2013/14 በጀት አመት 17.2 ቢሊዮን ብር እንዳተረፈ ቢገልጽም፣ የባንኩ ሰራተኞች እንደሚሉት ግን የተበላሸው ብድርና ያልተወረራደው ገንዘብ ግምት ውስጥ ሲገባ ባንኩ ያተረፈው ከ5 ቢሊዮን ብር አይበልጥም።

Wednesday, April 27, 2016

የቀድሞ የጋምቤላ ፕ/ት 9 ዓመት ተፈረደባቸው (በእጅ ጽሁፋቸው የጻፉትና ምስጢር የያዘው የክስ መቃወሚያቸው እጃችን ገብቷል)

(ዘ-ሐበሻ) የኖርዌይ ዜግነት እንዳላቸው የሚነገርላቸውና ደቡብ ሱዳን ላይ ታፍነው ተወስደው የታሰሩት የቀድሞው የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳደር አቶ ኦኬሎ አኳይ “አገርን ለመገንጠል” በሚል በቀረበባቸው ክስ የ9 ዓመት እስራት ተፈረደባቸው:: ኦኬሎ ከፍርድ በፊት ለሚዲያ ይድረስልኝ በሚል የላኩትና ለፍርድ ቤቱም በእጅ ጽፉፋቸው አስገብተውት የነበረው የክስ መቃወሚያ ዘሐበሻ እጅ ደርሷል:: ይዘነዋል::
ከኦኬሎ ጋር በተባባሪነት የተቀሰሱት ዴቭድ ኡጁሉ 9 ዓመት; ኡቻን ኦፔይ 7 ዓመት; ኡማን ኝክየው 7ዓመት; .ኡጁሉ ቻም 7ዓመት; ኦታካ ኡዋር 7ዓመት እና ኡባንግ ኡመድ 7 ዓመት ተፈርዶባቸዋል::

Wednesday, April 13, 2016

በጅንካ የመከላከያ ሰራዊትና ልዩ ሃይል አባላት ከፍተኛ ቅኝት እያደረጉ ነው

 የአካባቢው ነዋሪዎች እንደገለጹት በደቡብ ኦሞ በጅንካ ከተማና አካባቢዋ የመከላከያ ሰራዊት አባላት ከልዩ ሃይል አባላት ጋር በመሆን፣ በተለይ ከምሽቱ 2 ሰአት ጀምሮ በመኪኖች ላይ መትረጊስና ሌሎች ከባድ መሳሪያዎችን ደግነው ቅኝት በማድግ ላይ ናቸው፡፡ በዚህም የተነሳ የወጣቶች ነጻ እንቅስቃሴ የተገደበ ሲሆን፣ ነዋሪዎችም ጭንቀት ውስጥ ገብተዋል፡፡
ክትትሉ የተጀመረው በአካባቢው ከፍተኛ እውቅና ያላቸው የኦሞ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ኅብረት ም/ሊቀመንበርና የዞኑ ጽ/ቤት ቤት ኃላፊ አቶ ዓለማዬሁ መኮንን፣ አቶ አብረሃም ብዙነህ እና አቶ ስለሺ ጌታቸው መጋቢት 17፣ 2008 ዓም መታሰራቸውን ተከትሎና ፓርቲያቸው መሪዎቹና አባሎቹ ካልተፈቱ ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚጠራ መግለጫ ማውጣቱን ተከትሎ ነው፡፡
እነ አቶ አለማየሁ መኮንንን በሽብር ወንጀል ለመክሰስ የተደረገው ሙከራ ፣ ለምስክር የተዘጋጁ ሰዎች በሃሰት አንመሰክርም በማለታቸው ላይሳካ እንደሚችል ለኢሳት የደረሰው መረጃ አመልክቶአል፡፡
ለምስክርነት በቅድሚያ የታጩት የታሳሪዎች መኖሪያ ሲፈተሸ የነበሩ ስድስት ሰዎች ሲሆኑ ከእነዚህ መካከል አቶ መስፍን እርገጤ፣ አቶ ዓሊዬ ይታ፣ እና ወጣት ሃና ‹‹ከታሳሪዎች ቤት ክላሽንኮቭ ጠመንጃና ቦምብ በፍተሻ ሲገኝ አይተናል ›› ብላችሁ ከመሰከራችሁ ‹‹አዋሳ ወስደን ከመዝናናችሁ በተጨማሪ ለመቋቋሚያ የሚሆን ለእያንዳንዳቸው ብር 50 ሺህ፣ ይሰጣችኋል ››ቢባሉም የሃሰት ምስክርነቱን ኃሳብ ውድቅ ማድረጋቸውን ፣ ጉዳዩን በቅርብ ከሚከታተሉ የአካባቢው ነዋሪዎች ለማወቅ ተችሎአል፡፡
መስካሪዎች ‹‹ ከጂንካ ከተማ ህዝብ ጋር ከምንጋጭ ከነድህነታችን ከህዝብ ጋር መኖር እንፈልጋለን ›› ማለታቸውን የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ መስካሪዎቹ አዋሳ ለመሄድ ፈቃደኛ ያለመሆናቸውንና የዕለት ሥራቸውን ሰርተው ማደር እንደሚፈልጉ የገለጹ ሲሆን፣ ይህ ሳይሆን አዋሳ በግዳጅ ብንሄድ የተለየ እንደማንመሰክርና እየደረሰብን ያለውን ጫና ለህዝብ በአደባባይ ለማሳወቅ እንገደዳለን ማለታቸው ታውቆአል፡፡
በደቡብ ኦሞ መሬት ከወሰዱት ባለሃብቶች መካከል ከ98 በመቶ በላይ የሚሆነውን መሬት የወሰዱት የህወሃትና ከህወሃ ጋር ግንኙነት ያላቸው ሰዎች መሆናቸውን የሚያመለክት ጥናት በወጣ ማግስት እነ አቶ አለማየሁ መታሰራቸውን ኢሳት መዘገቡ ይታወቃል፡፡
መረጃው ከወጣ በሁዋላ የአካባቢው ነዋሪዎች በስፋት እየተነጋገሩበት ሲሆን፣ የዞኑ መስዳደርም ሆነ ክልሉ በጉዳዩ ዙሪያ ለህዝቡ ጥያቄ መልስ አልሰጡም፡፡
ሚያዚያ ፬( አራት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :

Friday, April 8, 2016

ትግሉ ሰፊ የምሁራን ተሳትፎ ይሻል!

April 8, 2016
def-thumbኢትዮጵያ በበብዛትም ይሁን በጥራት በውጭው አለምም ይሁን በሀገር ውስጥ የሚኖሩ ብዙ ምሁራን ያፈራች ሀገር ነች። በጅጉ የሚያሳዝነው ግን በሀገሪቱና በሕዝቧ ችግር ላይ ሀሳብ ሲሰጡ ፣ ባደባባይ ሲከራከሩና ሲታገሉ የሚታዩት በጅጉ ጥቂቶች ናቸው። ርግጥ ነው ተከታታይ መንግስታት በምሁራን ላይ ያደረሱት ጥቃትና ማግለል ከፍተኛ መሆኑ ይታወቃል። በዚህም ምክንያት ብዙዎች መከራን ከህዝብ ጋር ከመጋፈጥ ይልቅ አጎንብሶ ማሳለፈን የመረጡበት ሁኔታ አለ። ቁጥራቸው ጥቂት ያልሆኑም ለግል ጥቅማቸው ቅድሚያ በመስጠት ከጨቋኝ ገዥዎች ጋር በመተባበር የሚሰሩ መኖራቸውም አይካደም። አብዛኛው ምሁራን በተለይም በብዙ የሀገሪቱ ጉዳይ ላይ ጠለቅ ያለ እውቀት ያላቸው ጭምር ሀገሪቱን ከገባችበት ማጥ ለማውጣት በሚደረገው ትግል ውስጥ እየተሳተፉ አይደለም። ይህ ዛሬ ባለው ችግርም ይሁን በታሪክ ፊት አሳዛኝ ነው።
ሀገራችን ዛሬ መስቀለኛ መንገድ ላይ ነች። የተማሩ ልጆቿ መላ እንዲመቱ በመጠየቅ ላይ ትገኛለች። ይልቁንም በሀገራችን ያለው ችግርና ሀገሪቱ እየሄደች ያለችበት መንገድና አቅጣጫ በተለይ ምሁራንን እንቅልፍ ሊነሰ ይገባል። ዕውነታው ከዚህም አልፎ የሀገሪቱን አሳዛኝና አደገኛ ሁኔታ ለመቀየር በሚደረገው ትግል ውስጥ ከፍተኛ ተሳትፎ እንዲያደርጉ ግድ ይላል። የመንግስት ግፍና ሰቆቃ በበዛበትና የሀገራችን ሕልውና አደጋ ላይ በወደቀበት በአሁኑ ሰዓት ምሁራን ላለመሳተፍ ምክንያት ማቅረብ የማይችሉበት ወቅት ላይ ደርሰናል። እንደማንኛውም ሀገር ምሁራን የኢትዮጵያ ምሁራን በሀገራችን ውስጥ ሰላምና ዲሞክራሲ እንዲሰፍንና ፍትሕ የሰፈነበት ስርዓት እንዲመሰረት ሊሸሹት የማይገባ ትልቅ ሚና አላቸው።
ዛሬ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የሚኖሩ ዜጎች መንግስት በልማትና በልማት እያመካኘ የሚያካሂደውን ሰፊ ዝርፊያ እንዲሁም ወያኔ ሩብ ምዕተ አመት ሙሉ በብሄረሰብ እኩልነት ስም እየማለ የሚያደርሰውን ያንድ ብሄረሰብ ጉጅሌ የበላይነት ማስፋፋት እምርረው በመታገል ላይ ናቸው። መስዋዕትነቱን እየከፈሉ የሚታገሉትና የሚወድቁ የሚነሱት ወጣቶችና ምስኪን ገበሬዎች ናቸው። እነዚህ ወገኖቻችን ሕይወታቸውን ሳይቀር ሲገብሩ በየቀኑ እየሰማንና እያየን ነው። ይህንን የህዝብ ጥያቄና ትግል ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ምሁር ተመልካች ሆኖ ሊቀመጥ አይገባም። ትግሉን ከመምራት ጀምሮ እስከ ተራ ታጋይነት ባሉት ረድፎች ሁሉ ምሁራን ቀጥተኛ ተሳትፎ ሊያደርጉ ይገባል። ሰለትግሉ እቅጣጫም ሆነ ስለሀገሪቱ መጻዔ ዕድል ሃሳብ ማመንጨትና ማሰራጨት ይኖርበታል። ሀገራችን የደለቡ ችግሮቿን ተቋቁማ ፍትሕ ዲሞክራሲና እኩልነት የሰፈነባት ሀገር የሚያደርጋትን የምህንድስና ስራ አስቀድሞ ማሰብና ማመቻቸት ይኖርበታል። ርግጥ ነው ይህን መሰል ተሳትፎ የሚያደርጉ ምሁራን አሁንም አሉ። ቁጥራቸው ግን ሊሆን ከሚገባው ጋር ሲወዳደር በጅጉ አነስተኛ ነው።
ምሁርነት ከፍተኛ የትምህርት ደረጃ መቀዳጀት ብቻ እንዳልሆነ የታወቀ ነገር ነው። ምሁርነት ምሉዕ የሚሆነው መላውን የተፈጥሮ ከባቢ ከህዝብ ማህበራዊ ሕይወት ጋር አጣምሮ የሚያስብ አዕምሮን በዕውነት ላይ ለተመሰረተ ሀሳብና ዕውቀት ክብር መስጠትን ለተግባራዊነቱ መሟገትን የጨመረ ሲሆን ነው ። በመሆኑም ሁሌ እንደሚባለው ምሁርነት የጋን መብራትነት አይደለም። ምሁርነት በጨለማ ውስጥ ችቦ ሆኖ ብርሃን መፈንጠቅን ይመለከታል። ምስዋዕትነትንም ይጠይቃል።
ያለንበት ወቅት ለኢትዮጵያ ምሁራን ከፍተኛ ፈተናም ዕድልም ይዞ ቀርቧል። ይህ ልሽሽህ ቢሉት የማይሸሽ ፈተና ከመሆኑ ባልተናነሰ በታሪካችን እንድ ወሳኝ ምዕራፍ ላይ የጎላ አሻራን ለማኖርም ትልቅ የታሪክ ዕድል ነው። ይህ ፈተና ከፍተኛ ያርበኝነት ስሜትንና ሀላፊነት መውሰድን ይጠይቃል። አገር በተወሳሰበ ችግር ምክንያት ወደ አረንቋ እየገባች ምንም ሳይሰሩ መቀመጥ ወይም ዝም ብሎ ከመመልከት የበለጠ ለምሁር ሂሊና የሚከብድ ነገር ሊኖር አይችልም:: በጣም ላስተዋለ ሰው እንዲህ አይነት ዝምታ ሐጢያትም ነው። በእንዲህ አይነት ፈታኝ ወቅት የኢትዮጵያ ምሁራን ሀገሪቱን ወደተሻለ አቅጣጫ እንድትሔድ ላለመታጋል ምንም ምክንያት ማቅረብ አይችሉም። ሀሳብ የሚሰራጭባቸው የሀሳብ ክርክር የሚካሔድባቸው መድረኮች ፣ አደባባዮች ፣ የመገናኛ መሳሪያ አይነቶች የፖለቲካና የሲቪክ ማህበሮች ባገር ውስጥም በውጭም ያሉት መሳተፊያ ናቸው።
ድርጅታችን አርበኞች ግንቦት 7 ምሁራን በሰፊውና እንደየፍላጎቶቻቸውና ችሎታቸው ሊሳተፉ የሚችሉባቸው በርካታ የትግል መስኮች አሉት። የሀገሪቱን ውስብስብ ችግሮች ሊፈቱ የሚችሉ የጥናት ውጤቶች ፣ ሀሳቦች ፣ ምክሮችም ሆነ ቀጥተኛ የምሁራን ተሳትፎ ለማስተናገድ አመቺ ሁኔታ ያለበት ድርጅት ነን። ወደፊትም የምሁራን ተሳትፎ እንዲጎለብት ሁኔታዎችን ይበልጥ ለማመቻቸት እንሰራለን። ዽርጅታችን የሀገራችን ችግር የሚወገደውና ዲሞክራሲና የዜጎች እኩልነት የሚረጋገጠው በበሰለና ከተራ ዜጋ እስከ ብስል ምሁራን በሚያከሂዱት ክርክርና የበሰለ ሃሳብ ላይ ተመስርቶ መሆኑን ያምናል። አሁን ያለው የሀገራችን ምሁራን ተሳትፎ ደረጃ ሁላችንም ከምንጠብቀው በታች በጅጉ ያነሰ መሆኑ ሁላችንንም ከማሳዘን አልፎ የሚያስቆጭና የሚያንገበግብ ሆኖአል:: አገርና ህዝብ ድረሱልኝ እያለ በሚጣራበት በዚህ የታሪክ አጋጣሚ አይቶ እንዳላየ ሰምቶ እንዳልሰማ የተለያዩ ምክንያቶችን እየደረደሩ ማለፍ ይቻል ይሆናል። ይዋል ይደር እንጂ ለነጻነቱ ቀናዕ የሆነው የኢትዮጵያ ህዝብ የደረሰበትን አፈናና ጭቆና እምቢኝ ብሎ ነጻነቱን ሲቀዳጅ ግን ከታሪክ ፍርድና ከህዝብ ትዝብት ማምለጥ አይቻለም።
አርበኞች ግንቦት 7 በአገር ውስጥም ሆነ በተለያየ ምክንያት በአለም ተበትኖ የሚኖረው ኢትዮጵያዊ ምሁር ለወገን ደራሽነቱንና አለኝታነቱን አሁኑኑ ይወጣ ዘንድ ወገናዊ ጥሪውን ያቀርባል::
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

ለኮ/ል አታክልቲ ገ/ሚካዔል ልጅ ማሳከሚያ ከብረታ ብረት ኢንጂነሪግ ኮርፖሬሽን 3 ሚሊዮን ወጪ ተደረገ

የብረታብረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ለአንድ ባለስልጣን ልጅ ማሳከሚያ ሶስት ሚሊዮን ብር የህዝብ ገንዘብ ወጪ ማድረጉን ለኢሳት የደረሰው ሰነድ ያስረዳል። ኮሮፖሬሽኑ የወጣውን ገንዘብ በስሩ ያሉ ድርጅቶች በመዋጮ እንዲሸፍኑት መመሪያ ተላልፏል።
በብረታብረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን የሰው ሃይል አስተዳደርና ዕቅድ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር በኮ/ል ፅጌ አለማየሁ ስምና ፊርማ ህዳር 8 ፥ 2005 የተጻፈው ደብዳቤ ለኮ/ል አታክልቲ ገ/ሚካዔል ልጅ ማሳከሚያ የወጣው ወጪ በስሩ ያሉ ድርጅቶች በመዋጮ እንዲሸፍኑት ያዛል። ህክምናው በታይላንድ ባንኮክ መከናወኑንም ያስረዳል።
ጉዳዩ የኮ/ል አታክልቲ ልጅ ተማሪ ዮናስ አታክልቲ ታይላንድ ሄዶ የታከመበትን የህክምና ወጪ ይመለከታል በሚል ርዕስ የወጣው ደብዳቤ የሚከተለውን መልዕክት ይዟል። 
የብረታብንረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን የህወሃት ታጋዮች በነበሩት መኮንኖች የሚመራ ሲሆን፣ ዋና ዳይሬክተሩም አንጋፋ የህወሃት ታጋይ የነበሩት ብ/ጄኔራል ክንፈ ዳኘው መሆናቸው ይታወቃል።
ኮርፖሬሽኑ ከመንገዶች ባለስልጣን ለዕድሳት ብሎ የወሰደውን 88 ማሽነሪ ለትግራይ ክልል አሳልፎ መስጠቱ በአለም ባንክ ኦዲተሮች መጋለጡ በቅርቡ በሰነድ አስደግፈን መዘገባችን ይታወሳል። የማሽነሪዎች ዋጋም ከ65 ሚሊዮን ብር በላይ መሆኑን የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን ይፋ ማድረጉ ይታወቃል።
ለባለስልጣን ልጆች ማሳከሚያ በመስጠት የህዝብና የሃገር ሃብት በመመዝበር ላይ መሆኑ የብዙዎች ስጋት ሆኗል። በኢትዮጵያ ኦሮቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የአዲስ አበባ ሃገረ-ስብከት ስራ አስኪያጅ ሊቀማዕምራን የማነ ዘመንፈስቅዱስ ለልጃቸው ማሳከሚያ በሚል ለአዲስ አበባ አብያተክርስቲያናት ባቀረቡት ጥሪ ከአንድ ደብር ከአንጦጦ ኪዳነ ምህረት ቤተክርስቲያን ብቻ 500ሺ ብር እንዲወጣ መወሰኑ ባስነሳው ውዝግብ ጉዳዩ መጋለጡ ይታወሳል።
ፓትሪያርኩ በወሰዱት እርምጃ የማነ ዘመንፈስቅዱስ ከሃላፊነት የተነሱ ቢሆንም፣ የተዋጣውን ገንዘብ በተመለከተ ስለተደረሰው ውሳኔ የታወቀ ነገር የለም።
ኢሳት (መጋቢት 29 ፥ 2008)

በአምቦ ወህኒ ቤት አንድ ወጣት በደረሰበት አሰቃቂ በድብደባ ተገደለ

አምቦ ወህኒ ቤት ውስጥ የታሰረ አንድ ወጣት በድብደባ መገደሉን ወላጅ እናቱ ለኢሳት ገለጹ። ላለፉት 10 አመታት በወህኒ ቤት ውስጥ የቆየው ወጣት ጌጡ በቀለ ቶሎሳ፣ ህይወቱ ያለፈው ከአምቦ ወህኒ ቤት ቃጠሎ ጋር በተያያዘ እጅ አለበት በሚል በደረሰበት ድብደባ መሆኑም ተመልክቷል።
በፖለቲካ ሳቢያ ከ10 አመት በፊት ወህኒ ቤት መግባቱ የተገለጸው ወጣት ጌቱ በቀለ፣ እዚያው እያለ በመጣበት ተጨማሪ ክስ ወህኒ ቤት ውስጥ እንዲቆይ መደረጉን ከወላጅ እናቱ ገለጻ ለመረዳት ተችሏል። የመጣበትም ተጨማሪ ክስ በአካባቢው ከተገደለ የኦህዴድ ካድሬ ጋር በተያያዘ ሲሆን፣ ገዳዩ አንተነህ በሚል ተወንጅሎ መቆየቱንም መረዳት ተችሏል። Ambo
ወላጅ እናቱ በቅርቡ ወህኒ ቤት ሄደው ሲጎበኙ ጤነኛ የነበረው ጌቱ በቀለ ቶሎሳ በሳምንት ጊዜ ውስጥ ህይወቱ ማለፉን አስረድተዋል። ሆስፒታል መግባቱን ገልጾ በላከላቸው መልዕክት ሊጎበኙት ሲሄዱ አስከሬኑ መላኩ እንደተነገራቸው አስረድተዋል።
አስከሬኑን ለማግኘት የደረሰባቸውን መጉላላትም ያስታወሱት የሟች ወጣት ጌቱ በቀለ ቶሎሳ እናት፣ አስከሬኑ ሲደርሳቸው ከፍተኛ ድብደባ ያደረሱበት መሆኑን ገልጸዋል።
ሟች ወጣት በአካሉ ላይ በደረሰበት ድብደባ ከፊል ሰውነቱ በፋሻ መጠቅለሉንም ለኢሳት አስረድተዋል።
ኢሳት ( መጋቢት 29 ፥ 2008)

Wednesday, April 6, 2016

በስሉልታ ፌደራል ፖሊስ ከወጣቶች ጋር ተፋጧል – የአላሙዲ መኪኖች ተሰባበሩ * ፖሊስ እየተኮሰ ነው

Share0  0  0 
 Share0

Zehabesha News
 ከአዲስ አበባው ቤተመንግስት 28.4 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ሱሉልታ ከተማ የአካባቢው ወጣቶች ከፌደራል ፖሊሶች ጋር በፋጠጣቸው ተሰማ:: ከአካባቢው የሚመጡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት የሱሉልታ ወጣቶች የኢትዮጵያን ሕዝብ እየገደለ ያለውን የሕወሓት መንግስት በገንዘብ ይደግፋሉ ያላቸውን የሼህ መሀመድ አላሙዲ 3 መኪኖችን በድንጋይ ሰባብሯል::
በሱሉልታ ከተማ የሚገኘ አንድ የኤሌክትሪክ ትራንፎርሜሽን መፈንዳቱን ተከትሎ አካባቢው በፌደራል ፖሊሶች በመከበቡ የተነሳ ሕዝቡ ፖሊሶቹን አትወክሉንም; ከአካባቢያችን ዞር በሉ በሚል ተቃውሞውን ማሰማቱን ተከትሎ ፖሊሶች በወጣቶች ላይ ዱላ ሰንዝረዋል:: አንዳንድ ወታቶችም አጸፋውን በፖሊሶች ላይ ጥቃት ማድረሳቸውን የሚገልጹት የዘ-ሐበሻ የዜና ምንጮች ፖሊሶች በተኩስ የወጣቱን ተቃውሞ ለመበተን ሞክረዋል ብለዋል::
ይህ ተቃውሞ እየተደረገ ባለበት ወቅት በአካባቢው ይንቀሳቀሱ የነበሩ የሼህ መሀመድ አላሙዲ ንብረት የሆኑ መኪኖች በድንጋይ ሲደበደቡ የሦስቱም መኪኖች መስታወቶች መርገፋቸው ተሰምቷል::
በሌላ በኩልም በሰበታ የሁለተኛና የፕሪፓራቶሪ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ላይ ወታደሮች እርምጃ እየወሰዱ መሆኑን ከስፍራው የሚወጡ መረጃዎች አስታውቀዋል:
:(ዘ-ሐበሻ)

በጋምቤላ የእርሻ መሬት የወሰዱ 93 ባለሃብቶች መሬታቸውን እንዲመልሱ ተደረገ

በጋምቤላ ክልል የወረዳ አስተዳደሮች በህገወጥ መንገድ የእርሻ መሬት ተሰጥቷችኋል የተባሉ 93 ባለሃብቶች መሬታቸውን እንደመልሱ ተደረገ።
በህጋዊ መንገድ የእርሻ መሬቱን እደተረከቡ የሚገልጹት ባለሃብቶች በበኩላቸው መሬቱን ከክልሉ ባለስልጣናት በህጋዊ መንገድ ከተረከቡ በኋላ የፌዴራል ባለስልጣናት ርክክቡ ህገወጥ ነው ማለታቸው ተገቢ አለመሆኑን አስታውቀዋል።
በጋምቤላና ሌሎች ክልሎች ለውጭና ለሃገር ውስጥ ባለሃብቶች ሲሰጥ የቆየው ሰፋፊ የእርሻ መሬት በመንግስት ላይ ኪሳራን አስከትሏል መባሉን ተከትሎ የመሬት መስጠቱ ሂደት እንዲቋረጥ መደረጉ ይታወሳል።
መንግስት ደርሶበታል የተባለን ኪሳራ እንዲያጣራ የተቋቋመ አካልም በክልሉ ባለሃብቶች ያለግባብ ተሰጥቷል የተባለ 200ሺ ሄክታር መሬት እንዲመለስ ማድረጉን የግብርና ኢንቨስትመንት መሬት አስተዳደር ኤጀንሲ ማክሰኞ ገልጿል።
ይኸው ሰፋፊ የእርሻ መሬትም በ93 ባለሃብቶች ተይዞ የነበረ እንደሆነ የኤጀንሲው የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ዳንዔል ዘነበ ለሃገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን አስረድተዋል።
መሬቱን በህጋዊ መንገድ ከክልሉ እንደተረከቡ የሚገልጹት ባለሃብቶች በበኩላቸው በፌዴራልና የክልል መንግስታት በኩል የመናበብ ችግር በመኖሩ ሳቢያ በስራቸው ላይ ኪሳራ መድረሱን እንዳስታወቁ ከሃገር ቤት ከተገኘ መረጃ ለመረዳት ተችሏል።
የመሬት አስተዳደር ኤጀንሲ በበኩሉ በጎግና ዲማ ወረዳዎች ለ93ቱ ባለሃብቶች የተሰጠው መሬት ለኢኮኖሚ ዞን የተያዘ እንደነበርና ባለስልጣናት በህገወጥ መንገድ ርክክብ መፈጸማቸውን አመልክቷል።
በክልሉ ለበርካታ ባለሃብቶች ተሰጥቷል በተባለ ተደራራቢ የመሬት ርክክብ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በመቶ ሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ቢያበድርም ገንዘቡ የገባበት አለመታወቁን ይፋ ማድረጉ ይታወሳል።
በመንግስታዊ ባንኩ ላይ ደርሷል የተባለን ኪሳራ ተከትሎም ባንኩ ለሰፋፊ የእርሻ መሬቶች የሚሰጠውን ብድር ያቋረጠ ሲሆን፣ የፌዴራል መንግስትም የመሬት ቅርምት ነው የተባለውን መሬት ለባለሃብቶች የመስጠት ስራ እንዲቀር ወስኗል።
ከመንግስት ብድርን የተረከቡ በርካታ ባለሃብቶችም ከወሰዱት ብድር ጋር ከሃገር መኮብለላቸውን የልማት ባንኩ ሃላፊዎች በቅርቡ ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል።
ኢሳት (መጋቢት 27 ፥ 2008)

Tuesday, April 5, 2016

የዋዜማ ጠብታ- በኢትዮዽያ የሚንቀሳቀስ ኩባንያ በፓናማ (የሙስና ቅሌት ስነድ) ውስጥ ተጋልጧል

ከሁለት ቀናት በፊት በአለም አቀፍ ደረጃ ይፋ የተደረገውና ፓናማ ፔፐርስ (Panama Papers) በሚል የተሰየመው የሙስናና የገንዘብ ማሸሽ ቅሌት የተጋለጠበት ግዙፍ መረጃ የአለም የመገናኛ ብዙሀንን ስራ    አብዝቶባቸዋል።የእነማን ስም ተነሳ? የትኞቹ ኩባንያዎችስ አሉበት? የሚለውን ለማጣራት ጋዜጠኞች በር ዘግተው ስነዱን እየመረመሩ ነው።
በርካታ የላቲን አሜሪካ የእስያና የመካከለኛው ምስራቅ ሀገራት በቅሌት መዝገቡ በስፋት ተዳሰዋል። አፍሪቃም ከቅሌቱ አላመለጠችም። ባለሀብቶችና የፖለቲካ ሹማምንት በድብቅ በቤተሰቦቻቸው አልያም በቅርብ ወዳጆቻቸው ስም ከሀገር አሽሽተው የደበቁትን ገንዘብ የደበቀላቸው በፓናማ የሚገኝ ሞሳክ ፎንሲካ (Mossack Fonseca) የተባለ የህግ አማካሪ ነው። ይህ ተቋም ገንዘቡን የህግ ክፍተት ወዳለባቸው ትናንሽ ሀገሮች በማሸሽ የማማከር አገልግሎት ይሰጣል።የስዊስን ባንክ የመሳሰሉትን ደግሞ ለመሸጋገሪያነት ይጠቀምባቸዋል።
ባለሀብቶች ታክስ ለመሸሽና በስርቆት ያገኙትን ሀብት ወደዚህ ተቋም በመውሰድ ይሸሽጋሉ።የሩሲያው ቭላድሚር ፑትቲን ስማቸው እየተብጠለጠለ ነው። በስማቸው ሁለት ቢሊያን ዶላር በወዳጆቻቸው ስም ደግሞ የትየለሌ የሆነ ገንዘብ መዘረፉን ስነዶች ያመለክታሉ። የደቡብ አፍሪቃው ጃኮብ ዙማና የቀድሞ የመንግስታቱ ድርጅት ዋና ፀሀፊ ኮፊ አናን በወጣት ልጆቻቸው ስም የተቀመጠ ገንዘብ ተግኝቷል።
ይህ አይነቱ የገንዘብ ማሸሽ በተለየ ታክስ ላለመክፈል የሚደረግ ሲሆን በዘረፋ የተገኘንም ገንዘብ ለመሸሸግ ይመረጣል። ታዋቂ ስፖርተኞችና የፊልምና ሙዚቃ ኢንደስትሪው ባለፀጎች እዚህም እዚያም የራሳቸውም ሆነ የቤተሰቦቻቸው ስም መነሳቱ አልቀረም።
የእንግሊዙ ጠ/ሚ/ር ዴቪድ ካሚሮን አባት ስም ከዝርዝሩ መገኘቱ ፖለቲካዊ አተካሮ እንዳይቀሰቅስ ስጋት አለ። በሌሎች ሀገሮችም ቢሆን የፖለቲካ ቅሌቱ ህዝባዊ እንቅስቃሴ ያነሳሳ ይሆን ወይ የሚለውን ሁሉም በጉጉት እየጠበቀው ነው። ከመረጃው ገና የቀረ ስላለ የብዙዎች ስም በመጪው ሰነድ ውስጥ ይኖር ይሆናል።
በአለማቀፍ የምርመራ ጋዜጠኞች ህብረት International Consortium of Investigative Journalists (ICIJ)  እና በመገናኛ ብዙሀን እጅ የገባው ይህ ሰነድ ማንነቱን ባልገለፀ አካል ተጠልፎ የተገኘ ነው። ይፋ የተደረገው መረጃ 11.5 ሚሊየን ስነድ የያዘ ነው።
በኢትዮዽያ በማዕድን ዘርፍ ለመሰማራት ከአምስት አመት በፊት ፈቃድ ያገኘው የእስራኤሉ ኤንግልኢንቨስት በዚሁ የቅሌት ሰነድ ላይ ስሙ ተጠቅሷል። ድርጅቱ በእስራኤልና በአዲስ አበባ ተቀማጭ የሆኑ ባለሀብቶቹን ዝርዝሯል። ከተዘረዘሩት ግለሰቦች መካከል አንዱ የስሙ የመጀመሪያ ፊደል “Y” ብቻ በሰነዱ ላይ ስፍሯል። ይህ ምናልባትም የግለሰቡን ማንነት የበለጠ እንድንጠይቅ የሚገፋፋ ሳይሆን አይቀርም። ግለሰቡ ኢትዮዽያዊ ላይሆን ይችላል፣ ስሙን መሸሸጉ ግን ሰለዚህ የማዕድን ኩባንያ እንድንመራመር የሚጋብዝ ነው። የእንግሊዘኛውን ዋና መረጃ ከታች ይመልከቱት

የመልካም አስተዳደር ችግር ፈጣሪዎች ናቸው በሚል ከአዲስ አበባ በተባረሩ ፖሊሶች ምትክ አዲስ የቅጥር ምዝገባ እየተከናወነ ነው።

የአዲስአበባ ፖሊስ ኮምሽን ባወጣው ማስታወቂያ መሰረት ከመጋቢት 20 እስከ የካቲት 10 ቀን 2008 አም 10ኛክፍል ያጠናቀቁ ተመዝጋቢዎች በአካባቢያቸው በሚገኝ ፖሊስ ጣቢያ እየቀረቡ እንዲያመለክቱ ጠይቆአል።
በስርአቱ ውስጥ ከሙስናና ብልሹ አስተዳደር ጋር በተያያዘ በሀገር አቀፍ ደረጃ በሺ የሚቆጠሩ ፖሊሶችና አመራሮች እየተገመገሙ በመባረር ላይ ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ ክፍተቱን ለመሙላት አዲስ መቅጠር ማስፈለጉን ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ወገኖች ተናግረዋል።
በመንግስት ወጪ በቅርቡ የፒኤች ዲ ዲግሪያቸውን የያዙት የትራንስፖርት ሚኒስትሩ አቶ ወርቅነህ ገበየሁ ፣ ቀደም ሲል የፌዴራል ፖሊስ ኮምሽነር በነበሩበት ወቅት ከፍተኛ ሙስና በማካሄድ የሚታወቁ ሲሆን ፣ የእሳቸው ጉዳይ አስፈጻሚዎች አሁንም ባልተነኩበት ሁኔታ ተራ ወታደሩን በሌብነት አዋርዶ ማባረሩ በሰራዊቱ ውስጥ ከፍተኛ ቅሬታን ፈጥሮአል።
ኢሳት ዜና

Monday, March 28, 2016

የሰማያዊ ፓርቲ ዲሲፕሊን ኮሚቴ ሊቀመንበሩን ኢንጂነር ይልቃልን እና አቶ ወረታውን አባረርኩ አለ

(ምንሊክ ሳልሳዊ) – ጠንካራ ፓርቲዎችን ሰርጎ ገብ አስገብቶ በመበታተን ጠንካራ አመራሮችን በመወንጀል ፓርቲዎችን አዳክሞ ብመቃብራቸው ላይ ተለጣፊ ታማኝ ተቃዋሚዎችን የሚተክለው ኢሕኣዴግ በሰማያዊ ፓርቲ ውስጥ ገብቶ እየበጠበጠ እንደሚገኝ ከተለያዩ ምንጮች የሚወጡ ዘገባዎችን ተመልክተናል::
Yilikal Getenet
ፓርቲውን ለመቆጣጠር ፍላጎት ያለው ኢሕኣዴግ በሚደጉባቸው ሪፖርተር እና አዲስ አድማስ ጋዜጦች በኩል የፓርቲ አመራሮችን ስም ካለማስረጃ እና የፍትህ ውሳኔ ሲያጠፉ ከርመዋል::
በዛሬው እለት የተሰማው ዜና ደግሞ የሰማያዊ ፓርቲ ልሳን የነገረ ኢትዮጵያ አዘጋጅ በትዊተር ገጹ በዚህ መሰረት የድርጅቱ ሊቀመንበር ይልቃል ጌትነት እና ወረታው ዋሴ ከፓርቲው ሲባረሩ ወይንሸት ሞላ እና ስለሺ ፈይሳ ለ2 አምት ከማነኛውም የአመራርነት ቦታ ታግደዋል።ሰማያዊፓርቲ ሊቀመንበሩንና የቀድሞው የፋይናንስ ኃላፊን ከፓርቲው አባረረ። ሆኖም የሊቀመንበሩ መባረር ተግባራዊ የሚሆነው ከጠቅላላ ጉባኤ በኁዋላ መሆኑን እርምጃውን የወሰድው የዲስፕሊን ኮሚቴ ገልጹዋል ሲል ጽፏል::

Wednesday, March 23, 2016

ቤተ አምሃራ የወልቃይት ጠገዴ ጠለምትን ትግል በማስመለከት ብአዴንን አስጠነቀቀ – “የአማራ ህዝብ ቁጣ ለመትረፍ ከህዝባችሁ ጎን ቁሙ”


Share1  519  1 
 Share1

bete amhara
ቀን: መጋቢት 13 2008 ዓ. ም
ወቅታዊውን የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ የማንነት ትግልን በማስመልከት ከቤተ አማራ የተሰጠ መግለጫ ፦
የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ የትግሬ – ወያኔ ሽፍታ ስርዓት በጉልበት የጫነባቸውን ባዕድ ማንነት በመቃወም የተፈጥሮ ማንነታቸው የሆነውን አማራነት ጥያቄ ያቀረቡት እጅግ ሰላማዊ በሆነ መንገድ እንደነበር ይታወቃል::
ይህም የታላቁ አማራ ህዝብ ለዘመናት የኖረበትን ከፍተኛ የሞራል ደረጃ ማሳያ ሆኖ ተመዝግቧል:: ምንም እንኳ በወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ ላይ የደረሰው እና አሁንም በመተግበር ላይ ያለው ግፍ እና የዘር ማጥፋት እርምጃ ለበቀል ሊያነሳሳ የሚችል የአረመኔዎች ተግባር ቢሆንም ሰፊው የአማራ ህዝብ በአስደናቂ ትዕግስት እና ሆደ ሰፊነት ለሁለት አስርት አመታት ጉዳዮን ታግሶት ቆይቷል::
ሰላማዊ እና ዲሞክራሲያዊ የመብት ጥያቄዎች የሚያስደነግጡት የትግሬ-ወያኔ አስተዳደር የእኛን ወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ የማንነት ጥያቄ ለማዳፈን ያልጎነጎነው ሴራ የለም:: እስራት፣ ማዋከብ፣ አስገድዶ መድፈር፣ ማፈናቀል እና ግድያ በተለያዮ ጊዜያት በወገኖቻችን ላይ የተፈጸመ እና እየተፈጸመ ያለ ሲሆን በተቀነባበረ ወያኔያዊ ሰላማዊ ሰልፍም ያለምንም ሃፍረት በሃገሪቱ ቴሌቪዥንም በተዘገበ ፕሮግራም በወገኖቻችን ላይ የተለመደውን የጅምላ ግድያ እርምጃ ይወሰድ ዘንድ ሲለፍፉ ሰፊው የአማራ ህዝብ በአግራሞት ተከታትሎታል:: ከሶስት ቀናት በፊት በዳንሻ እና ሶሮቃ ተጠናክሮ የቀጠለው አፈና፣ እስር እና ግድያም የዚሁ በዕብሪት የተሞላው የፀረ – አማራ እቅዳቸው አካል ነው::
በመሆኑም የትግሬ-ወያኔ አስተዳደር ይህ ሁለቱን ህዝቦች ወደማይበርድ እልቂት ሊወስድ ከሚችለው ሰይጣናዊ ድርጊት ባስቸኳይ በመታቀብ የሚከተሉትን እርምጃዎች እንዲወስድ ቤተ አማራ በጥብቅ ያሳስባል::
1. በደህንነት አሽከሮቻችሁ ታፍነው የተወሰዱት የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ የማንነት ኮሚቴው አባል አቶ ሊላይ ብርሃኔ እና ሌሎች አማሮች ያለምንም ማንገላታት ባስቸኳይ እንዲፈቱ::
2. የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ የማንነት ጥያቄ የማይቀለበስ የመላው አማራ ጥያቄ መሆኑን ተገንዝባችሁ ከያዛችሁት እራስን የማጥፋት አካሄድ እንድትቆጠቡ::
3. በተለያዩ ቦታዎች በአማራ ወገኖቻችን ላይ እየተፈጸመ ያለውን ማንገላታት፣ እስር እና ግድያ ባስቸኳይ እንዲቆም::

ወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ ሆይ ፦

የመላው ቤተ አማራ ወገኖቻችሁ ማንነታችሁ ማንነታችን፣ ጉዳታችሁ ጉዳታችን ፣ ጠላታችሁ ጠላታችን ብለን በተጠንቀቅ ከጎናችሁ የተሰለፍን መሆናችንን ልናረጋግጥላችሁ እንወዳለን::

መላው አማራ ሆይ ፦
የትግሬ – ወያኔ የደገሰልንን የዘር ማጥፋት ዘመቻ ለመመከት በጀግኖች አባቶቻችን መንፈስ በአማራነት ተደራጂተን በአንድነት እንድንቆም ጥሪያችንን እናስተላልፋለን::
በዕርቅ ስም የህዝባችንን ትግል ለመቀልበስ ለምትንቀሳቀሱ ሃሳዊ ሽማግሌዎች እና የሃይማኖት አባቶች ፦
ሰላማዊ የሆነውን የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራነት ጥያቄ ለማዳፈን እውነተኛ ባልሆነ የሽምግልና ስም እየተንቀሳቀሳችሁ ያላችሁ ግለሰቦች ከአንዴም ሁለት ጊዜ ድብቅ ማንነታችሁን ህዝባችን ስልተረዳ ከዚህ መጥፎ ግብራችሁ እንድትታቀቡ በጥብቅ እናስጠነቅቃለን::
እንዲሁም የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራ ለሃይማኖቱ ያለውን ቀናዒነት ተጠቅማችሁ የህዝባችንን የማይቀለበስ የማንነት ጥያቄ ለማዳከም እየጣራችሁ ያላችሁ የስርዓቱ ጥገኛ የሃይማኖት መሪዎች ከዚህ መሰሪ ተግባራችሁ እጃችሁን እንድትሰበስቡ በጥብቅ እናሳስባለን።
ለብአዴን ባለስልጣናት እና ካድሬዎች ፦
ከመጨረሻው የአማራ ህዝብ ቁጣ ለመትረፍ ከህዝባችሁ ጎን ከመቆም ውጭ ሌላ አማራጭ እንደሌላችሁ አውቃችሁ አስላለፋችሁን ታስተካክሉ ዘንድ በጥብቅ እናሳስባለን። ታላቁ የአማራ ህዝብ እንደ ንስር ሃይሉን ያድሳል ! ቤተ አማራ ወደፊት !

Wednesday, March 2, 2016

የህወሃት ልዩ ነፍሰ ገዳይ ሠራዊት አመሰራረት። የገዳይ ቡድኑ አጋዚ እና የእናት እንባ


agazi
የህወሃት ልዩ ነፍሰ ገዳይ ሠራዊት አመሰራረት። የገዳይ ቡድኑ አጋዚ እና የእናት እንባ
የእግሊዝኛው ጽሁፍ አዘጋጅ ፡ዓለም ማሞ
የአማርኛው ተርጓሚ፡ቢላል አበጋዝ
“ፔንታጎን ያሰለጠናቸው የኢትዮጵያ ሠራዊት ፤ክፉውን አጋዚ የተሰኘውን ልዩ ኅይልም ይጨምራል።”
–ጄረሚ ስከሂል
ኢንተር- ሴፕት ኤንድ ናሽናል ሴኩሪቲ ለተባለው ጋዜጣ መስራችና ቃል አቀባይ ከአሜሪካ መንግስት ክፍተኛ ምክር ቤት የፍርድ ኮሚቴ ዘንድ ቀርቦ ከሰጠው የምስክርነት ቃል የተወሰደ ጥቅስ። ዲሴምበር 9 ፣2010
ታሪኩ እነሆ
ከእድሜዋ በላይ የጠናች መስላ ትታያለች።በአካል ያያት ስድሳ ዓመት ሞልቷታል ብሎ መገመት ይችላል።እውነቱ ግን አርባ ዓመትዋ ብቻ ነው።
“ወታደራዊው መንግስት ስልጣን ከመያዙ ሁለት ዓመት በፊት ነው የተወለድኩት” ትላለች ታሪክ እየጠቀሰች።የተጨማደደው ቆዳዋ፤ማዲያቷ እና ሽበትዋ መከራን ያሳለፈችን እናት ታሪክ ይናገራሉ።ያለፉት አስር ዓመታት በችግር የተሰቃየችባቸው ናቸው። “የበኩር ልጄን ከአስር ዓመት በፊት ቀበርኩ፤እኛ ተቃዋሚዎች አቸንፈን ድምጣችንን በቀሙን ጊዜ” አለች ወደ አድማሱ ቃኝታ ከተራሮቹ ሰው ብቅ የሚል እንደሁ ትጠብቅ ይመስል።
“እንዴት ሞተ?” ብዬ ጠየቅኋት ላለፉት አስራ አምስት ደቂቃዎች ከማታው ውርጭ ላይ ከቆየንበት ውጭ ወደቤት እየተከተልኳት።
“በጠራራ ጸሃይ ከሚወደው ጓደኛው ጋር ነው የገደሉት።አንዲት ቦታ፤ በአንዲት ቀን ነው አዲስ አበባ ላይ የተገደሉት።” አለች በተጎሳቀለው ፊትዋ ላይ እምባዋ እየወረደ።ምሬትዋንና ያለችበተን የከፋ ሃዘን ጥልቀት በቃላት ለመግለጥ ይከብዳል። ከተቀመጥኩበት ብድግ ብዬ እጆችዋን ይዤ ካጠገብዋ ቁጢጥ አልኩ። “ማን ገደላቸው ?” ብዬ ጠየቅኋት።ትክዝ ብላ ቆይታ ወደበሩ ራመድ፡ ራመድ ብላ በሩን ከዘጋችው በኋላ ሚስጥር እንደምትነግረኝ ሁሉ ዝቅ ባለ ድምጥ “አጋዚ። አጋዚ። ነው የገደላቸው” እያለች የሟች ልጆችዋን ፎቶግራፎች ሳም ሳም አድርጋ እንዳያቸው ሰጠችኝ።ለትምህርት ምረቃ ቀን የተነሷቸው ነበሩ።ምስላቸው በፈገግታ ተሞልቷል።ምኞትና ተሰፋ ይታይባቸዋል።ፎቶግራፎቹ በእምባዋ ርሰዋል የንባዋ ዘለላ በፎቶ የሚታየውን የልጆችዋን ፈገግታ ሲሸፍነው ሀዘንዋን የሚጋሯት መስሎ ታየኝ። ሙታንና ቁዋሚዎች አብረው የሚያለቅሱበት አገር። በምናቤ ልጆቹ ቤቱ ውስጥ ያሉ መሰለኝ።በናትና ልጅ መሃል ሞትም የማያስቀረው ውህደት በማህፅንና በእትበት መሃከል ያለው ቁርኝት ይሆን ? እንጃ። ብቻ የልጆቹ ውቃቢና የዓፍላ መንፈሳቸው ክቤቱ ውስጥ አለ።ካደጉበት።ከምዬ ቤት።ገና ባጭር ሳይቀጩ ከነበሩበት።ከኪሴ መሃረብ አውጥቼ እንባውን ከፎተግራፎቹ በዝግታ ጠረግሁ።በጥልቅ አዘኔታ ሳያቸው ወንድሞቼ፤የወንድሜ ልጆች፤ያጎት ያክስቶቸ እንዲያው የናቴ ልጆች መስለው ታዩኝ።በህይወት ባሉበት ጊዘ አግኝቻቸው ባላውቅም የማውቃቸው መሰሉኝ።የኔ የራሴን ያለፈ የልጅነቴንና የወጣትነት ዘመን ከፊቴ ደቀኑብኝ።ወጣትነቴን፤ፍርሃት አልባነቱን፤ለፍትህ፤ለነጻነት፤በቁርጠኝነት ተከራካሪነት መቆሙን።
ዲሞክራሲ! ለምእተ አመታት እውን ያልሆን ስንቀርበው የሚርቀን የኔ ትውልድ ህልም፤ያለፈው ትውልድም ህልም፤የዛሬው ትውልድም። “አዬ እርግማን” ብዬ ለራሴ አጉተመተምኩ።
ለመሄድ ስነሳ አዘንተኛዋ እናት እቅፍ አረገችኝና እባክህ ደግመህ መጥተህ ጠይቀኝ አለችኝ።እምባ እየተናነቀኝ ይሁን መጣለሁ። እጠይቅሻለሁ አልኳት።ስለያት ብቸኝነትዋን አሰብኩት።የሞቀ የደመቀ ሁለት ልጆችዋ ይቦረቁና ይጫወቱ የነበረበትን የዛሬውን ኦና ቤትዋን አሰብኩት።የናትን ሃዘን ጥልቀቱን እንድረዳው፤እንዲሰማኝ ሞከርኩ። የእናትን ሃዘን ፤የዘጠኝ ወር ቤትን ህመም ፤ ክናት ሌላ ማን ሊረዳው? አልኩ ለራሴ።
አጋዚ የሚለውን ስም በተደጋጋሚ ሰምቸዋለሁ።ኢትዮጵያ ውስጥ ሰዎች ስለ አጋዚ የሚናገሩት ልክ እንደ ውጭ ወራሪ ሀይል አድርገው ነው።የዚህ ቡድን ሰለቦችና ተግባሩን ያዩት እንደሚናገሩት “ግኡዝ ገዳይ ሮቦቶች፤ ምንም ልዩነት የማያደርጉ ትንሽ ከትልቁ መለየት ህጻናት ከአዋቂ፤ወጣት ሽማግሌ፤ ሴት፤ ወንድ፤ የታጠቀ ወይ ጀሌ አንዱንም የማይመርጡ።ጨፍጫፊ።ግፍ መስራቱን ይወዱታል ቢባል ከውነት የራቀ አይሆንም።
አንድ የፋሺት ጣሊያ ወረራ ጊዜ የነበሩ አርበኛ አጋዚን ከጣሊያኑ ጊዜ ካራብኘሪ ጋር ያመሳስሉታል።
“ቋንቋቸው ግራ ነው።ባህልና ወግ ግዳቸውም አይደል።ባሻቸው ጊዜ መጥተው ወንዶችን፤ልጆችን መንጭቀው ይሄዳሉ።ሲሻቸው እዚው ረሽነው ይሄዳሉ። መንደር ቀበሌ ከተማ ይወርራሉ።አየህ አጋዚ ልክ እንደ ጣልያን ካራብኘሪዎች ነው።” የአረጋዊው የነጣው ረጅም ጢም፤የተሸበሸበው ግንባራቸው ብሩህ አይኖቻቸው ምስክርነት የቆሙ ይመስላሉ።
“ታውቃለህ እንዲህ ያለ በገዛ ህዝቡ ላይ የሚጨክን መንግስት ኖሮን በታሪካችን አያውቅም። ካራብኘሪዎችን ምን እንዳደረግናቸው ልንገርህ።” አሉ በኮራ ድምጻቸው “የእግዜርን እርዳታ ይዘን ከአርበኞች ጋር ሁነን ነቅለን ጣልናቸው።” የሚነደው ያገር ፍቅራቸው እንደ እሳት ወላፈን ሙቀቱ እየተሰማኝ። “አጋዚዎችንም ዋጋቸውን እንሰጣቸዋለን።አዲሱ ትውልድ የኛን አርበኝነት ተዋርሷል።የጊዜ ጉዳይ ነው።አገራችን ነጻ ትወጣለች።” አሉ ምርኩዛቸውን ጠበቅ አድርገው እየጨበጡ።የታሪክ ምጸት ቢሆንም የአጋዚን ከጣሊያን ካራብኘሪዎች ማነጻጸር አሁን ብቻ አይደለም የሰማሁት።በስልጣን ላለው መንግስት ተወዳዳሪ ለሌለው ጭካኔ ማመሳከሪያ በመሻት ነው።
ባገሪቱ የትኛውም ክፍል ህዝባዊ እምቢተኝነት ወይም አመጽ ሲነሳሳ ከየት መጣ ሳይባል አጋዚ ከቸች ብሎ የአፈናና የግድያ ተግባሩን ያከናውናል።ብዙ ተመሳሳይ የአጋዚን ዘግናኝ ተግባራት፤ኢሰባዊ ድርጊቶችም የሚገልጡ በርካታ ምስክርነቶች ሰምቻለሁ።ሁለት ወንዶች ልጆችዋን ለአጋዚ የገበረችውን እናት ካነጋገርኩ ወዲህ ግን አስተሳሰቤ ተለወጠ።ሀዘንም ዋጠኝ።ከዚህ ሌላስ ምን ግፍ ተሰርቷል?ምን ግፍስ ይሰራ ይሆን? እያለ አእምሮዬ ወተወተ።የዚህን የገዳይ፤አፋኝ ቡድን አሳዛኝ ድርጊት በሚቻለኝ መጠን ለማጋለጥ ቁርጠኛ አደረገኝ።
አጋዚ የሚለው ስም በኢትዮጵያ ፍራትና ሽብርን ይፈጥራል።ልክ ካራቫን ዴላ ሙኤርቴ (የሞት ቅፍለት) ተብሎ በቺሌ ላቲን አሜሪካ ይታወቅ እንደነበረው አይነት ነው።ይህ ቡድን አውጉስቶ ፒኖቼ የተባለው ወታደራዊ አምባ ገነን በ1973 ዓም መፈንቅለ መንግስት እንዳካሄደ ያቋቋመው ነው።ሌላው ተመሳሳይ ደግሞ ጄኔራል ሆዜ አልቤርቶ ሜድራኖ ያቋቋመው ኦርጋኒዛሲኦን ዴሞክራሲያ ናሺናሊስታ የተባለው የኤል ሳልቫዶር (ላቲን አሜሪካ) ገዳይ ሰራዊት ነው። ይህ ሰራዊት በስውር የሚያግት፤በህይወት ፈራጅ፤ሰቆቃ ፈጻሚ ነበር። ለማንም መንግስትን ለተቃወመ ወይንም ተቃውሙዋል ተብሎ ለሚጠረጠር ቡድን ወይም ግለ ሰብ ያለ ምህረትና ሰባዊነት የግፍ ቀንበሩን ያሰፈረ ቡድን ነበር።
አጋዚ ምስጢራዊ ራስ ገዝ ተጠያቂነቱ ቱባ ለሆኑት እፍኝ የማይሞሉ የህወሃት አመራሮች ነው።አጋዚ የተሰየመው ከህወሃት መስራቾች አንዱ በነበረው ዘሩ ገሰሰ የትግል ስሙ አጋዚ ነበርና።በውነተኛ ወታደራዊ አደረጃጀት ሲመዘን አጋዚ የግል ጦር፤ቅጥረኛ በጦር ቱጃሮች (war lordes) የግል ጥቅማቸውን ለመጠበቅ የሚቆሙትን ዓይነት ነው።የእዝ ሰንሰለቱ ከቋሚው ዘረኛና በዘር ከተዋቀረው የህወሃት መደበኛ መከላከያ መዋቅር ውጭ ነው።የአጋዚ መኖር ዋነኛ ምክንያት ወያኔ ኢሃዴግን በስልጣን ማሰንበት ነው።መንደርም በእሳት ተለኩሶ ይውደም፤ንጹሃን በጥይት ይፈጁ፤ ቀዬዎች የሽብር አምባ ይሆኑ፤ወያኔ ብቻ ይሰንብት። የአጋዚ መኖር ለዚህ ነው።አጋዚ ቀድሞ ሲመሰረት “ጸረ ዓለማቀፍ ሽብርተኛ” የሚል ጭንብል ነበረው። ይህ የሆነው የምእራብ አገር መንግስታትን ለማማለልና ደስ ለማሰኝት አልፎም ድጋፍ፤ስልጠና እና ትጥቅም ለማግኘት ነበር።ቍም ነገሩ ግን አገር በቀል የሆኑትንና ለዲሞክራሲ ፤ ለፍትህና ለነጻነት ራእይ የሚደረጉ ትግሎችንና እቢተኝነትን መደምሰስ ነው።
በዚህ ጉዳይ ላይ ጥቂት መርማሪ ጋዜጠኞች ስለ አጋዚና የውጭ ድጋፉ ጠይቀዋል።ይህን ግፈኛ ቡድን ማነው የሚያስታጥቀው ማንስ አሰለጠነው እያሉ።ከኒህ ጋዜጠኞች መካከል ጄረሚ ስከሂል ተቀዳሚው ነው።የዩ ኤስ አማሪካን ተመሳሳይ ሚና በአፍጋኒስታን፤ በማሊ፤ በሶማሊያ፤በየመን መርምሯል። በዲሴምበር 9 ቀን 2010 ዓም ለአሜሪካ ምክር ቤት በዝርዝር ምስክርነት ሰጥቷል።ምስክርነቱ ሰው አልባ የሚበር አውሮፕላንን እቅስቃሴ፤የዩ ኤስ አሜሪካንና የሶማሊያ ጎሳ ጦር አበጋዞች ጋር ግንኙነት አካትዋል። “ሽብርተኝነትን መዋጋት” በሚል ሰበብ እንዴት አሜሪካ እንደ አጋዚ ያሉ የገዛ አገራቸውን ዜጎቸ የሚያሸብሩ ወታደራዊ ተቋሞችን መደራጀት ልታግዝ እንዴት እንደቻለች ጠይቋል። እንደ ሚስተር ሺል ጥናት “የዩ ኤስ አሜሪካን ልዩ ወታደራዊ ቡድን ለረጅም ጊዜ የአጋዚን ሰራዊት ሲያሰለጥን ኖርዋል” የስከሂል የጥናት ጭብጥ እንደ ህውሃት ካሉት ጋር መቧደን የዘለቄታው ጉዳቱን ለአሜሪካና ለአገራችንም የሚያስከትለውን ጉዳት ማመላከት ነው።
ቃሌን ጠብቄ የሁለቱ ልጆች እናት የወላድ መሃንዋን ልጠይቃት ተመለስኩ።ጭጋጋማ ቀዝቃዛ ምሽት ነበር።ከጓሮዋ ካለችው ትንሽ ያትክልት ስፍራ እየቆፋፈረች ነበረ።”በልጆቼ ሃሳብ የተጨናነቀውን አእምሮየን ቢያስታግስልኝ ብዬ እማስናለሁ።” አለች እጅዋን እየጠራረገች። ክበሩ መግብያ ስደርስ ጠበቅ አድርጋ አቀፈችኝ። የናት ፍቅር ሙቀቱ እየተሰማኝ ወደቤቱ ውስጥ ተከተልኳት።
“እግዜር ይባርክህ ልትጠይቀኝ በመምጣትህ።” አለች ወደ ማድቤቱ እያመራች። “ሻይ አፈላልሃለሁ” አለች።
“አመሰግናለሁ” ብዬ መለስኩ።
ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ በእጅ በተሰራ ቅርጫት ብስኩት፤ ሻይ በፊንጃል ይዛልኝ መጣች።ስለ ብዙ ነገሮች አወራን።”ዛሬማ ብዙ እናቶች ለሞቱ ልጆቻችው ጥቁር ይለብሳሉ” አለችኝ አንዳንዶቹን በስም እየጠራች።
“ዛሬ እኮ ጨለማ ዘመን ነው።ጓደኞቸ፤መንደርተኞቸ፤የከተማውም ሰው አንድ ሰው ቢያንስ ተገሎባቸዋል” አለችኝ።
ደግሜ ልጠይቃት የመጣሁት ስለሟች ልጆችዋ ለመጠየቅ የሷንም መጽናናት ላውቅ ብዬ ነው።እንቅልፍ አጥታ እንደሰነበተች እንዲያው ድክም ብሏታል።ትንሽ ተኝታ ታድር እንደሁ ጠየቅኋት። “ሽለብ ሲያገኝ ልጆቼ ከፊቴ ድቅን ይላሉ።ከትምርት ቤት ሲመጡ፤ያዘዝኳቸውን ሲከውኑ፤የትምህርት ቤት የቤት ስራቸውን ሲሰሩ።እንቅልፍ የለኝም።ደህና እንቅልፍ የተኛሁበት ምሽት ይናፍቀኛል።” ጥልቁ ሃዘንዋ፤አንዱ በሌላው ላይ የተደራረበው መከራዋ ህወሃት የፈጸመውን በደሎች ያመለክታሉ።ፈተናዋ አድክሟታል።
“የት ነው ልጆችሽ የተቀበሩት ?” አልኳት
“ተዚህ ግድም።ሩቅ አይደለም። በግር ያስኬዳል።በሰንበት ሁሌ ልጆቼን ላጫውት እሄዳለሁ” አለች።
“ዛሬ ትወስጅኛለሽ?” አልኳት
“አዎ! እወስድሃለሁ” እያለች ጥቁር ጥለት ነጠላዋን ተከናንባ “ተከትለኝ” አለችኝ። “በዚህ ጋ” ስትል ተከትያት ለአስራ አምስት ደቂቃ በደረቀው ሳራማ ሜዳ ላይ የግር መንገዱን ተከትለን ተጓዝን።ከሩቁ የሚግጡ ከብቶች ይታዩኛል።ጥቂት ሄደን ቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ደረስን።ጥቂት ጸሎት አድራጊዎች ተውጭው ይታያሉ ሌሎችም እየመጡ ነበር።ተገረገራው ስትደርስ አማተበችና እየሰገደች ጸለየች። እኔም እንደስዋ አደረግሁ። ጥቂት ራመድ እንዳለች ከበተ- ክርስትያኑ ደቡባዊ ጠርዝ ልጆችዋ ካረፉበት ደረስን። ጠጋ ስንል ንግግርና ልቅሶ ተደባልቀው እንሰማለን።
“እዚህ ነው ትኝት ያሉት።ልክ ከቤታቸው አብረው በልጅነታቸው ተቃቅፈው ይተኙ እንደነበረው፤አበቦቼ፤ልጆቼ” እያለች ፊትዋ ላይ ያለውን እንባ ጠረገችው።የራሴን እንባ እየታገልኩ እሷን ላጽናናት ሞከርኩ።ትንሹ ሲገደል ገና አስራ ስድስት ዓመት እንደነበረና ሰላማዊ ሰልፍ ሲካፈል እንደተገደለ ነገረችኝ። “ልክ እንደኔው ልጆቻችው በአጋዚ ጥይት የረገፉባቸው እናቶች እጅግ ብዙ ናቸው።” አለች ጉዞአችንን ወደ መጣንበተ ማምራት ስንጀምር።
“እንደምሰማው አጋዚዎች የሰለጠኑት በአሜሪካኖች ነው።ይህ እውነት ነው?” ብላ ጠየቀችኝ።አጥብቃ ነው የጠየቀችው ድምጽዋ ንንዴትም ብሶትም የተቀላቀለበት ይመስላል።
“አዎን ተመሳሳይ ዜና ሰምቻለሁ” ብዬ መለስኩላት።
“ለምን ልጆቻችንን የሚገድል ታጣቂ ቡድን ያሰለጥናሉ? ሳስብ የነበረው አሜሪካኖች ደግ ሰዎች ናቸው ብዬ ነበር። አዛኞችም ናቸው ብዬ ነው።”
“የአሜሪካ ህዝብ አይደለም።ይህ የፖለቲከኞች ውሳኔ ነው።” ብዬ ተገቢውን መለስኩላት። ትንሽ ቢያጥናናት ብዬ።
“ምን አልባት እንዳንተ የተማሩ ሰዎች የኛን በደል ለአሜሪካ ፖለቲከኞች ማድረስ አለባቸው። አጋዚ የሚባለው ልጆቻችንን መግደል እንዲያቆም።” አለች።
ለአሜሪካ ፖለቲከኞች ፤ለአሜሪካም ህዝብ ለዓለምም ሁሉ መልክትዋን ለማድረስ ቃል ገባሁላት።
ለመሄድ ስነሳ እንደምትማጠነኝ ሁና ወዳይኔ ብረቱ እያየች፤
“እባክህ በደላችንን ዓለም እንዲያውቀው አድርግ።አጋዚን አሰልጥነው ማስታጠቃቸው፤ በጅምላ ገዳዮችን ማሰልጠናቸው መሆኑን ይወቁት።አንድ ብቻ ሳይሆን ሁለት ልጆችዋን የተቀማችዋን እናት ታሪክን ንገራቸው።የወላድ መካንን እናት ምን ይሏታል? መካን የሆንኩት ሁለቱን ባንዴ አጋዚ ሲቀማኝ ነው።” አለች።
እኔ ለዚህ ሁሉ ጥያቄዎችዋ መልስ የለኝም።መልስም የምትጠብቅ አይመስለኝም።እንደው ሀዘንዋ ይውጣላት ብላ እንጂ።ምናልባት ሁለቱንም።እኒህ እለት ተእለት የማብሰለስላቸው ጥያቄዋች ናቸው።እስተማውቀው ድረስ ጥያቄዎቹ በሺ የሚቆጠሩ እናቶች ባገሩ በሞላ የሚጠይቋቸው ጥያቄዎች ናቸው።
ምስኪንዋን እናት ተሰናብተን መንደሩን ለቀን ስንጓዝ አይኖቼ አካባቢውን አማተሩ።የሚጫወቱ ልጆች አይታዩም።በማሳው ላይም ገበሬዎች የሉም ።መንገደኛም አይታይም።ህይወት እርጭ ብሎ፤ታግቷል።ተሩቅ የተኩስ ድምጥ ይሰማኛል።ማን ይሆን ባለሳምንት? ሌላ ወጣት? ወንድ ?ሌላ ወጣት ሴት?ሽማግሌ ማን ይሆን? ማነው ባለተራ ? ማን ይሆን የአጋዚ እራት ብዬ ተከዝኩ።
ባልጋዬ ጋደም ብዬ ያን ማታ የዚህን ጭካኔ መነሻ ልደርስበት አሰብኩ።ዘመናዊ ስልጣኔና ተቋም አቀድ የሆነ አረመኔያዊ ጥፋት በንጹሀንና ባልታጠቁ ህዝቦች ላይ! ሃሳቤ ከቦታ ቦታ ተንክራተተ፤ከአንድዋ እናት እምባ ወደ ሌላዋ። ከአንዱ አባት ምሬት ወደ ሌላው።ሸለብ ያረገኝ ብዬ ባስብ አእምሮዬ እምቢ አለ።“ሽለብ ሲያደርገኝ ልጆቼ ድቅን ይላሉ” ብላ ያለችው ደግሞ ደጋግሞ ባሳቤ ይመጣል።ልጠይቃት መሄዴ ሃዘንዋን አባብሶት ይሆን? ብዙ ተገላብጨ እንቅልፍ እምቢ ሲለኝ ተስፋ ቆረጥሁ።አጣጥፌ ከደብተሬ ያኖርኩትን የተጣጠፈ ወረቀት ሳብ አደረግሁት።የጥንቱ ሮማዊ ገጣሚ ጋየስ ቫሌሪየስ ከታለስ (84᎔54 ከክርስቶስ ልደት በፊት)ግጥም ነበር። ለሟች ወንድሙ የገጠመው፤
“በባእድ ባህሮች ቀዘፋ፤ ባልታወቁ ወደቦች ለቀናት በባህር ስጓዝልህ
ከዚህ የመጣሁት ለሽኝት ነው የናቴ ልጅ ላንተው ስንብት፤
ለሞትከው የቋሚን የመጨረሻ ስጦታ ይዥልህ
ቃሌ ከንቱ ነው ትቢያ ለሆነው ሰው።
አይ ወንድምየ ይኸው አንተን ነጠቁኝ
አንተን አብሮ አደግ ወንድሚን ቀሙኝ!
በጨካኝ እጃቸው ቀጠፉህ እኔንም በሀዘን ወጉኝ።
ይሄው ተዝካርህ ድሮም ለሄደ ድንግጉ
ትዝካርህን እነሆ በማእርጉ
የወንድምህ እምባ ያራሰውን
ውሰድ አድናቆቴን በሞቴ የእምባየን ንዳድ ስንብቴን”
ግጥሙን በህወሃቱ አጋዚ ለተገደሉት ሁሉ ደጋግሜ አነበብኩት።ደጋግሜ ባነበብሁት ቁጥር አገሩን ማሰስ አማረኝ። እያንዳንድዋን አጋዚ ልጇን የቀማትን እናት ላናግር።ላዳምጣቸው፤ ሀዘናቸውን እካፈል ብዬ።ስሜቴና ፍላጎቴ ቢገፋፉኝም በተግባር ማዋሉ አቀበት መሆኑ አልጠፋኝም።የአጋዚ ግድያ ከመብዛቱ የተነሳ ቁጥሩ አያሌ ነውና በጥቂት ዓመታት ላዳርስ የምችለው ጥቂቶችን ብቻ ነው።ጥቂቶችን ብቻ።ጠዋት ሲነሱ ባዶ ወንበሮችን የሚያዩትን እናቶች። ከትምሀርት ቤት የቀሩባቸውን፤ለሰርጋቸው ያልበቁላቸውን፤አያቶች ያደርጉናል ብለው ይጓጉላቸው የነበሩትን።
ቆይቶ አእምሮዬ ተረጋግቶ አሰበ።አገሩን አስሼ የእናቶችን የሃዘን ህመም ሁሉ ማዳመጥ ወሰንኩ።የግል የምስጢር ፍላጎቴም ይሆናል የአባቴን አገር፤ውቡን አገር ያያት የቅማያቴን አገር ላይ።ቀኑ፤ቦታው፡ሰአቱ፡ምክኛቱ ወይ ሰውዬው የተለየ ይሆናል ወይ ጠመንጃውን የተኮሰው ሰውዬ አንድ አይሆን ይሆናል። የናቶች መሪር ሀዘን ግን ከሰሜን ተራሮች ይሁን ከምዕራብ ጥቅጥቅ ጫካ ፤ከሜዳማው አገር ይሁን ከደቡቡ ሳራማ መሬት፤ክምስራቅ፤ከከተማ ይሁን ባላገር የትም ቢሆን የእምዬ ሀዘን ያው ነው።እርር፤ድብን ነው።የዘጠኝ ወር ቤት ንዳድ።
ላሁኑ ስለማውቃት እናት መናገር መርጫለሁ።ስለተዋወቅኋት ደስታና ክብር ስለሚሰማኝ እናት።በስም ልጠራት የማልችለው እናት።የሁለት ልጆችዋ ምስል በአእምሮዬ ታትሞ የቀረው።ጀምበር በወጣች ቁጥር እኔን ወጥረው ይይዙኛል።ሁሌም ለፍትህ ቁም።ለስልጣን ለሹመት ሳይሆን እያሉ። ይህ ደግሞ ላደርግ ከምችለው ትንሹ ነገር ነው።
ደራሲውን ለማግኘት
alem6711@gmail.com

Thursday, February 18, 2016

ቻርል ዳርዊንና የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሁኔታ


Darwin-and-land-to-the-tiller
ቻርል ዳርዊንና የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሁኔታ
ቢላል አበጋዝ
ዋሽግቶን ዲ ሲ፣ሐሙስ ፣ ፌብሩወሪ 18 ቀን 2016
የታላቁ ሳይቲስት የቻርል ዳርዊን 207ተኛው ልደቱ በዚህ ወር ተከብሯል። እሱ ካልው አንዱ ነገር
“ከዝርያዎች መካከል ጠንካራው አይደለም ኗሪነቱ ቀጣይነት ያለው(እማይመክነው:እማይጠፋው)። እጅግ ብልሁም አይደለም። ለለውጥ ዝግጁ የሆነው እንጂ”
ቻርልስ ዳርዊን 1809
መግቢያ
ቻርል ዳርዊን የሳይንስ ብቻ ሳይሆን የፖለቲካም ሰውም የነበረ ቢሆን ኖሮ የኢትዮጵያን የፖለቲካ ሁኔታ መረጃ ተሰብስቦ ቀርቦለት ምን ታስባለህ ቢባል በኦሮሞ ክፍለ አገር እየሆነ ያለው ዓመጽ የኢትዮጵያ ህዝቦችሁሉ የሚያደርጉት አገር አቀፍ ዴሞክራሲያዊ ትግል አካል ነው። ይህ እንዴት ይህ ተሰወራችሁ? ብሎን ይታዘበን ነበር እላለሁ። የሰውን ልጅ አስተሳሰብ፤ሳይንስን እንዳለ ቀየረው የሚባለውን መላምቱን ለመቅረጽ ዳርዊን የፈጀበት ጊዜ እኛ ወያኔን ስናስታምም የፈጀነውን ዘመን ያንሳል።
ለውጥ ሲመጣ እያየነው ለውጡን ወያኔ ሲያውገረግረው እኛ ግን አስተሳሰባችንንና መንገዳችንን መቀየር ካቃተን ለውጡን ወያኔ እንዲጠቀምበት አደረግን ማለት ነው።በዚህ እራሳችንንም አገራችን ኢትዮጵያንም እንበድላለን ማለት ነው። አዲስ ሁኔታ ሲከሰት ወዲያው ሁኔታውን አገናዝበን አስተሳሰባችንንም ቀይረን ዛሬ የሚጠይቀውን አቅጣጫ መቀየርን፤ማረምን፤ዝግጅትን ማድረግ እስካልቻልን ወያኔን መርታት ዳገት መሆኑ ግልጥ ነው።ጥንካሬም ብልሃትም እያለን እንዴት ወያኔ ሰነበተን? ካልጠየቅን ወያኔ አፍዝ አደንግዝ እንዳስደገመብን ያለ ነው። በኦሮሞ ክፍለ አገር እየሆነ ያለው ዓመጽ ልድገመው የኢትዮጵያ ህዝቦች ሁሉ የሚያደርጉት አገር አቀፍ ዴሞክራሲያዊ ትግል አካል ነው።
ትንታኔ
በዚህ ጽሁፍ የቻርል ዳርዊንን የአራዊትና እጽዋትን ዝርያ አመጣጥና ዝምድና ገላጭ መላምቱን የማቅረብ ዓላማ የለኝም።ከላይ የጠቀስኩት የዳርዊን አባባል የሚለግሰንን ብልሃት ለዲሞክራሲያዊ ትግላችንም ምን ይዘይድበታል ለማለት ብቻ ነው።
በወጣትነት ዘመኑ ቻርል ዳርዊን ለአምስት ዓመታት በመርከብ ዓለምን ዞሮ የጽዋትና የእንስሳትን መረጃና ናሙናም ሰብስቦ ለሃያ ዓመታት ከተመራመረ በኋላ ዝርያዎች በቀጣይነት ዘራቸው የማይጠፋው [survival] ተፈጥሮ ራሱ በደነገገው መሰረት የገጠማቸውን ነባራዊ ለውጥ ለመቀበል የተመቻቹትን ብቻ የሚመርጥ ስርዓት ስላለ መሆኑን በገናናው መላምቱ ሲያስረዳ፤ ለውጥ ለመቀበል ያቃታቸው፤መራባትም ያልሆነላቸው ዘራቸው መክሰሙንም በመላመቱ አካቶታል።
ህወሃት መሩ መንግስት ልክ እንደወታደራዊ ደርግ አዋጅ፤ህገ መንግስት፤ብሄር ገለመሌ እያለ ቀስ ብሎ ስልጣን ላይ ጉብ ሲል፤ፊቱ ለሚደቀኑ የነበሩ ተለዋጭ ሁኔታዎች መልስ እያዘጃጀ እራሱንም ለለውጥ እያመቻቸ ነበር። ዛሬም ይህንኑ ያደርጋል። እስታሁንም ለውጥ ሲመጣ ቢደናገጥም ተንገዳግዶ ይቆማል።ለለውጥ ዝግጁ መሆንና፤ፊታችን የሚከሰተውን ለውጥ ማየት እየተሳነን ህወሃትን አቸናፊ እናደርገዋለን። ይህንን ቀጥዬ ላስረዳ።
ኢትዮጵያን ሙሉ በሙሉ ለመቆጣጠር ወያኔ ገና ከተማ ሳይገባ ማን ብርቱ ተቃውሞ እንደሚያደርግበት በመረዳት የኅይልም የፕሮፓጋንዳውንም በትር አማራው ብሄር ላይ ያሳርፍ ነበር።ህወሃት ጋር የተደለሉ ኦሮሞዎች ሎሎችም እየተባበሩ።ከአማራውም ከሌሎች ብሄሮችም ተጨምረው አድር ባዮችን በጥቅም አሰልፎ ሲያበቃ የራሱን በፖለቲካ ስልጣን መደርጀትን የዝምድና ሀረግ በማድረግ ሰንብቶበታል። ይህ ዛሬም ያለ ዝምድና ነው።ይህን ዝምድና ስር ነቀል ለውጥ ብቻ የሚሽረው ነውና ህወሃት እስታለ ደግሞ ይቀጥላል።ህወሃትን ዲሞክራሲያዊው ትግል በድል ሲሽረው ወያኔ ጋር አብሮ ታሪክና ትዝብት ይሆናል። ባጭሩ ወያኔ ዝግጅት አድርጎ ሲገባ ህዝባዊ ዴሞክራሲያዊ ሀይሎች አልተዘጋጁም ነበር።ይሄው ሃያ አምስት ዓመታ እየተቆጠሩ ነው።
እንዳአሁኑ የወጣት ተማሪዎች እንቅስቃሴ የኦሮሞ ብሄረሰብ በብዛት በሚኖርባቸው የኢትዮጵያ ክፍላተ አገር እንደሚካሄደው በሌሎቹም ቦታዎች እየተነሱ ተራ በተራ መመታታቸውን አይተናል።ህወሃት አገር አቀፍ እንዳይባልበት እጅግ ሲጥር የመጣውን ለው የሁላችን የጋራ ነው ለማለት ተስኖን በመደናገር ራሱ ህወሃት ያለው ደግመን [ትቀብለን] አመጹን “የኦሮሞ”፤ “የአማራ” እናደርገዋለን።ባጭሩ ቻርልስ ዳርዊን እንደሚለው ሀይል ቢኖረንም ለውጡን ለመጠቀም ራሱን ያመቻቸው ህወሃት ሆኖ እናገኘዋለን።
በኦሮሞ ክፍለ አገር ዛሬ ተቀጣጥሎ እየነደደ ያለው ዓመጽ እንዴት ተከሰተ?የህዝባዊ ብሶቱ መነሻ ምንድን ነው?በሌሎች የኢትዮጵያ ክፍላተ አገራት ከተነሱት ዓመጾች በምን ይመሳሰላል?እንዴት ሊራመድ ይችላል?ወያኔን ለማንበርከክ ምን ቀጥሎ ምን ይደረግ እንደማለት ህወሃት ለመጣው ለውጥ የሰጠውን ስያሜ ውጠን “የኦሮሞ ክልል” የዚያ ክልል የሚል ታርጋ እንለጥፍበታለን።ለህወሃትም የሌለውን ብላተኛነት አክለንለት ከናካቴው አመጹን ወያኔ በውስጥ እጅ ሆን ብሎ በራሱ ሰዎች እንዳስነሳው የምናስብም አለን። የተንኮል ቅንብር (Conspiracy Theory) ድረስ የምንሄድና ወጣቱ በደሙ የከፈለበትን መና ለማድረግና ህወሃትም ለመርታት አስቸጋራ መስሎ እንዲታይ ያለማስተዋል እንናገራለን።ህወሃት ጠንካራ አይደለም።ብልሃትም የለውም።የለት ተለትዋን ለማድረግ ግን ጮሌ ነው። እስታሁን በራሱ ላይ ህዝባዊ አመጽ ሆን ብሎ የሚዶልት አምባገነን ታይቶ የሚታወቅ አይመስለኝም።ህወሃት ግን የተፈጠረውን ሁኔታ ሊጠቀምበት የማያደርገው የለም ማለት ይቻላል።በግልጹ ለመናገር አማራው ኦሮሞውን፤ኦሮሞው አማራውን እንዲጠላውና እንዲጠራጠረው በመሆኑ የህወሃት ፍላጎት እደተመኘው የምንሆንለት እራሳችኑ ነን።ተመቸነው ልበል ወጣቶች እንደሚሉት ?ለውጥን ፈርተን መለወጥ አቅቶን እንዴት ወያኔን ለማሰናበት እንችላለን?
ነገ የአማራው ህዝብ በብዛት በሚኖርበት ክፍለ አገር አመጽ ቢቀጣጠል።የጋምቤላውና የአፋሩ እንደቀድሞው ቦግ ሲል የህወሃት መሩን መንግስት መግለጫ ተቀብለን የምናስተጋባ ከሆነ ብልሃትም ጉልበትም የኛ ቢሆንም ወያኔ የለመደውን ግዜያዊ ድል አግኝቶ ቀጠለ ማለት ነውና፤ ሲሆን ለውጥ ሳይመጣ ቀድመን እናስላ ካልሆነ ለውጡ፤አመጽ ሲከሰት ሌላ ስም ሳይሆን አገር አቀፍ ዴሞክራሲያዊ ትግል መሆኑን ኢትዮጵያ አገሬ የምንል ይህን ስያሜ እንጂ የወያኔን አናስተጋባ።ሌላ ምሳሌ ”ኢትዮጵያ ትፈራርሳለች” ሲል የወያኔ ተረት ተረት “ወያኔ ስንት ቦታ ተሰንጥቆ ይፈርሳል ?” ብለን ይህን ሂደት ለማፋጠን ምን ይደረግ እንበል።ዛሬ ኢትዮጵያ ለለውጥ ዝግጁ ናት የምሁራንዋ ዝግመት እንጂ !” ይህን እናስብበት::
የኢትዮጵያ ህዝቦች የሚያደርጉት አገር አቀፍ ዴሞክራሲያዊ ትግል ያቸንፋል!
የፖለቲካ መሪዎች አሁኑኑ ይፈቱ!
የሃይማኖት መሪዎች አሁኑኑ ይፈቱ!
የታሰሩ ጋዜጠኞች አሁኑኑ ይፈቱ!
ለወጣቶች ግድያ ህወሃት እንጂ ማንም ተጠያቂ አይደለም !
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!

Thursday, February 4, 2016

የሀገር አድን ጥሪ ለወጣቱ!(ከአርበኞች ግንቦት7 ወጣቶች መምርያ )

ማክሰኞ ፣2 ፌብሩወሪ 2016
12042873_868355303254893_5731700769108826326_nወጣቶች በሃገራችን ላይ የተጫነብን የወያኔ የመርገምት አገዛዝ ያጎሳቆለን፤ በኑሮ የተበደልንና በሰላም ለመኖር ያልታደልን ፍጡሮች ብንሆንም ህዝባችን ነጻነቱን ሲቀማ፣ መብቱ ሲደፈር፣ ክብሩ ሲዋረድ ከዳር ቁመን የምንመለከትበት አንዳች ምክንያት ሊኖረን አይገባም። ወቅቱ ለነፃነታችንና ለመብታችን ባላንጣ የሆነውን አምባገነን የወያኔን ስርዓት ፊት ለፊት ተጋፍጠን፣ በትግላችን ደቁስን ማንነታችንን የምናስመስክርበት ወቅት እንጂ በፍርሃትና በዝምታ ተውጠን ወደኋላ የምንልበት ስዓት አይደለም። ደግሞም እኛ ወጣቶች ለመብት እና ነፃነታችን ተፈጥሮ የለገሰችንን እምቅ ኃይልና ጉልበት ተጠቅመን በቁርጠኝነት ተነስተን ካልታገልን የሥርዓቱን አምባገነናዊ የጭቆና አገዛዝ በፍርሃትና በዝምታ እንደተቀበልን ተደርጎ መወስዱ የማይቀር ነው።
ከምንግዜውም በላይ እኛ ወጣቶችን ዛሬ ሁለት አበይት ጉዳዮች በጉልህ ያሳስቡናል፤ ሊያሳስቡንም ይገባል። እነዚህም ሃገራችን ያለችበት አሳሳቢ ሁኔታና የኛ የተተኪው ትውልድ የወደፊት ተስፋ ምን ሊሆን ይችላል? የሚሉት ናችው። በቀደመው ጊዜ በሃገራችን የተፈራረቁት አምባገነን ገዥዎች ለወጣቱ ተስፋና የተሻለ ነገር ከመስጠት ይልቅ በጠላትነት ፈርጀው በሽብር እየገደሉና ጥቃት እየፈጸሙበት ሲያሳድዱት ኖረዋል። የወጣቱ ሰቆቃ አሁን በወያኔ ዘመን ደግሞ እጅግ በጣም በከፋ ሁኔታ ተባብሶ ቀጥሏል።
የወያኔ መሪዎች ለኢትዮጵያዊያን ወጣቶች ማዕከላዊን፡ ቃሊቲን፤ ሽዋሮቢትን፣ ዝዋይን እና የመሳስሉ የሰቆቃ እስር ቤቶችን ሲያሰፉ እንጂ የሥልጠናና የምርምር ተቋም ሲያድሱና ሲገነቡ ለማየት አልታደልንም። የሚገነቡ የትምህርት ተቋማትም ለሥርዓቱ የእድሜ ማራዘሚያ እንጂ የእውቀት ማስጨበጫ ተቋም እንዳልሆኑ ተግባራቸውንና ውጤታቸውን መመልከት ይቻላል። በአደባባይ ያለፍትህ የሚገደለው ወጣት ባንክ ሲዘርፍ ተገኘ፣ ወንጀል ሲሰራ ተያዘ የሚሉ የሀሰት ምክንያቶች እየተለጠፉበት ያለኃጢአቱ የሀሰት ስም በመቀባት ዳግም ይገሉታል።
የነገ ሀገር ተረካቢ ትውልድ ከሚፈራበት የትምህርት ተቋም ድረስ በመግባት የአማራ ህንጻ፣ የኦሮሞ ህንጻ፣ የትግሬ ህንጻ…ወዘተ እያሉ የትምህርት ሥርዓቱን ከጠባቡ የፓለቲካ ግባቸው ጋር በማያያዝ በነገ ተስፋችን ላይ ዘምተው የልዩነት ግድግዳ ባሳፋሪ መልክ እየገነቡ ቀጥለዋል። አላማው ደግሞ በጎስኝነት በሽታ ተውጠን ከእህቶቻችንና ከወንድሞቻችን ጋር እየተባላንና እየተገዳደልን የምንኖርበት ሲኦል ለመፍጠር መሆኑ አያጠያይቅም። በዚህም ሳቢያ ብሔራዊ ሰሜታችን እየደበዘዘ ሄዷል። ብሔራዊ ሰሜት ከሌለን ደግሞ አገር አለን ማለት ጨርሶ የሚታስብ እንደማይሆን ግልጽ ነው።
በነገራችን ላይ ዛሬም ድረስ ወያኔዎች ለእድገትና ለልማት መዘጋጀታችውን እየደሰኮሩ ህዝብን በማታለል የስልጣን ዘመናቸውን ለማርዘም መውተርተራቸውን አላቆሙም። በየጊዜው ኢትዮጵያ ተመነደገች፤ ልማቱ ተፋጥኗል እያሉ በሃሰት ህዝብን ለማወናበድ ይሞክራሉ።እውነታው ግን በእጅጉ ተቃራኒ መሆኑን የህዝቡን የኑሮ ሁኔታን በመመልከት መረዳት ይቻላል። ዛሬ የፋሽስቱ ወያኔ አገዛዝ በፈጠረው የተወሳሰበ ችግር በሀገሪቱ የወጣት ሥራ ፈትና ተጧሪ ሞልቶና ተትረፍርፎ በሚታይበት፤ ሥራ የማግኘት እድል በፓለቲካ ታማኝነት ብቻ በሆነባት ሃገርና ወያኔ የፓለቲካ ሥልጣኑንና ወታደራዊ ኃይሉን ተጠቅሞ የሀገሪቷን ሀብት እያጋበስ በሚዘርፍበት ሁኔታ ላይ ቆመን ልማትና እድገት ማለት ለእኛ ለኢትዮጵያውያን ተራ ማጭበርበሪያና ዲስኩር ካልሆኑ በስተቀር ፈጽሞ ትርጉም የሚሰጥ አይደለም።
ለነገሩ ወያኔ ከመጀመሪያው ጀምሮ ያዘጋጀልን ቃሊቲ፤ ማዕከላዊ፤ ሁርሶን፤ ሽዋሮቢትንና የመሳሰሉትን የማሰቃያ ማጎሪያዎች መሆኑን የተረዳን ስለሆነ በዚህ የምንደናገር አይደለም። ለዚህም ነው በአሁኑ ወቅት እኛ ወጣቶች ተሰባስበንና ተደራጅተን ከመታገል ውጪ ሌላ ምርጫ የለንም ብለን በድፍረት የምንናገረው።
አምባገነንነት ስርዓት ካልተገታ የአገር ሰላም ሆነ የህዝብ ህልውና እና አንድነት ዋስትና አያገኝም። በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ሥልጣን የጨበጡት ወንበዴ ግለሰቦች የኢትዮጵያ ህዝብን ሀብት እየተቀራመቱ ለግል ጥቅማቸው የሚያውሉ፣ ህዝቡን የሚገሉ፤ የሚረግጡና የሚበድሉ በተለይ ደግሞ ለባእድ ጥቅም የተገዙ ናቸው። እነዚህ ግለስቦች ብሔራዊ ስሜታችውን አሽቀንጥረው የጣሉ፤ የራሳችውን ባህል፤ ወግ፤ ታሪክና ሕዝብ አምርረው የሚጠሉ ከራሳቸውና ሥልጣን ላይ ካስቀመጧቸው መንግሥታት ጥቅም ውጪ ሌላ ምንም የማይታያቸው ናችው።
ታዲያ የሃገራችን ህልውና ከመቼውም በላይ ለከፋ አደጋ ተጋልጦ ባለበት በአሁኑ ወቅት በተለይ የእኛ የወጣቶች ግዴታና ድርሻ ምን መሆን አለበት ብለን ራሳችንን መጠየቅና ብሎም መልስ ለመስጠት መዘጋጀት ሀገራዊ ግዴታንና ኃላፊነትን ለመወጣት የመጀመሪያው እርምጃ መሆን ይኖርበታል።
ጭቆናንና በደልን በመታገል ረገድ ደግሞ የቀደምት የታላላቅ ወንድሞቻችንና እህቶቻችን አኩሪ ገድል ለዛሬው ትግላችን ትልቅ የትምህርት ማእከል ሆኖ ያገለግለናል። ሀገራችን ከኋላቀር ሥርዓትና ከብልሹ አገዛዝ ተላቅቃ፤ ድህነትን አሸንቀጥራ ጥላ በልማት ጎዳና እንድትራመድ፤ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እውን እንዲሆን፤ ማህበራዊ ፍትህ እንዲስፍን ባጠቃላይም ተጨባጭና ዘላቂ ለውጥ በሃገራችን እንዲመጣ ጽኑ እምነት ሰንቀው ለሕዝባዊ ትግሉ ሕይወታቸውን መስዋእት በማድረግ ሲታገሉ የነበሩ ጀግና ወጣቶች እንዳሉ ታሪክ ያስገነዝበናል።
ዛሬም ጭምር ግንባራችውን ሳያጥፉ መስዋእትነትን በመክፈል እያስመስከሩ ያሉ መኖራቸውን ስንመለከት ጀግና የሚያፈራው ጀግናን ነውና እኛም ወጣቶች አንገታችንን ቀና አድርገን ዛሬም እንደ ትናንቱ ለሃገራችንና ለህዝባችን ነፃነት መታገል ብሔራዊ ግዳጃችን ብቻም ሳይሆን ታላቅ ክብርም ጭምር መሆኑን ተገንዝበን ለሞት ሽረቱ ትግል በቁርጠኝነት መነሳት ይኖርብናል። ከፊታችን ለሚጠብቀንና ሃገራችን እያሰማች ላለው የሀገር አድን ጥሪ መልስ ለመስጠት እኛ የኢትዮጵያ ወጣቶች ከሃገር ቤት እስከ ውጪው አለም ድረስ የተቀናጀና የተቀነባበረ ንቅናቄ በመፍጠር ምላሽ ልንሰጥ ይገባል።
በኅብረትና በጽናት ከታገልን ደግሞ የወያኔን የሰቆቃ አገዛዝ አሰወግደን የሕዝባችንን ሮሮ የማናስቆምበት እና ተጨባጭ ለውጥ በሀገራችን ለማምጣት የማያስችለን አንዳች ምድራዊ ሃይል እንደማይኖር በእርግጠኛነት መናገር ይቻላል። ዛሬ በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ እንዳለ ብልጭ ብልጭ እንደሚል ኮኮብ ብንመስልም በርግጠኝነት ነገ ከፀሐይ ደምቀን ከአሽዋ በርከትን የምንታይበት ጊዜ ይመጣል፤ እየመጣም ነው።
በመጨረሻም የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ ወጣቱን ትውልድ መብቱንና የዜግነት ክብሩን ለመጎናጸፍ እንዲችል ብሎም የሀገር እና የወገን ነፃነትን ለማምጣት ወያኔን ታግሎ ማሸነፍና ከስልጣኑ ማውረድ ግድ ነው ብሎ በጽኑ ያምናል። በአገር ውስጥም ሆነ በመላው ዓለም ተበታትኖ የሚገኘውን ወጣት በአገሩ ተከብሮ እንዲኖር የተለየና የተቀደሰ አማራጭ አለው። ይኸውም እየተደራጁ መታገል፣ እየታገሉ መደራጀት ነው ብሎ ንቅናቄያችን ያምናል።
የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ የነደፈውን ጊዜ የማይሽረውን ሁለገብ የመታገያ ስልትና አላማን ከግብ ለማድረስ ትግልን በጽናት መቀጠል የሚለው መርሁ ሲሆን ተደራጅቶ በጽናት መታገልን በተግባር ለማዋል ደግሞ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ወጣት ንቅናቄውን እንዲቀላቀል ጥሪ ያደርጋል። ተደራጅቶ ሊያጠፋን የተነሳን ጠላት በተደራጀ ሃይል ማንበርከክና ከስር መሰረቱ ማስወገድ ይቻላልና። ስለዚህ የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ በአረመኔው የወያኔ አገዛዝ ላይ የሚካሄደውን ትግል አጠናክሮ በመቀጠል በአገር ውስጥ ወጣቱን በህቡዕ ከማደራጀት ጀምሮ በውጭው ዓለም በየአህጉሩ በተዋቀሩ የንቅናቄው መዋቅሮች አማካኝነት ወጣቱን አደራጅቶ በማንቀሳቀስ አስፈሪ የሆነ የነፃነት ማዕበል ፈጥሯል። አሁንም የንቅናቄውን ዓላማ የሚደግፉና በነፃነት ትግሉ ለመሳተፍ የቆረጡ ወጣቶች እንዲቀላቀሉ የአርበኞች ግንቦት7 ወጣቶች መምርያ በድጋሚ ሃገራዊ ጥሪ ያቀርባል!
ፈሪዎችንና ባንዳዎችን ወደ ጎን በመተው እውነተኛ ታጋዮችን ይዘን ትግላችንን እንቀጥላለን!!!
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!