Monday, November 16, 2015

በረሀብ ለተጠቁ ወገኖቻችን እንድረስላቸው !!!

November 14, 2015
def-thumbበወቅታዊ ሁኔታ ላይ የአርበኞች ግንቦት 7 የአቋም መግለጫ
የኢትዮጵያ ሕዝብ ዳግም ለአስከፊ ረሀብና ችጋር ተጋልጧል፤ ስፋት ጥልቀቱ በ70ዎቹና 80ዎቹ ከነበሩት ጋር ይስተካከላል ተብሎ ተፈርቷል። ከአሁኑ ሰው በረሀብ መሞት መጀመሩ ከአራትና አምስት ወራት በኋላ የሚመጣውን አደጋ ከባድነት መገመት ያስችላል።
ለአስር ተከታታይ ዓመታት ከአስር በመቶ በላይ ዓመታዊ የኢኮኖሚ እድገት በማምጣት ዓለምን እየመራን ነው የሚለው ዓይን ያወጣ ውሸት፤ “ድህነትን ተረት እናደርጋለን” የሚለው ጉረኛ መፈክር፤ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ራድዮ “የህዳሴ ብስራቶች”፣ የአባይ ግድብና የከተማ ባቡር ግንባታ ዜናዎች ለኢትዮጵያዊው አርሶ አደር ቁርስ፣ ምሳና እራት አልሆኑም።
“አድገናል”፣ “ተመንድገናል”፣ “በምግብ ራሳችንን ችለናል” ሲል የከረመው የህወሓት አገዛዝ የረሀቡ ዜና አፈትልኮ ሲወጣ እና የዓለም መገናኛ ብዙሀን መነጋገሪያ ሲሆን የተራበውን ወገናችንን ለማብላት ከመሯሯጥ ይልቅ ተፈጥሮ ላይ ማላከኩን ተያይዞታል። ከዚህ አልፎ ዓመታዊ ድግሶቹ እና ለባለሥልጣናቱ የሚሰጡ ጥቅማጥቅሞች ጉዳይ ከረሀብ በላይ አሳሳቢ በመሆኑ 15 ሚሊዮን የሚገመት ሕዝብ በሞት አፋፍ ላይ እያለ የአገሪቱ ሀብት ለድግስና ፈንጠዚያ እንዲሁም ለእያንዳንዱ ባለሥልጣን ቤተመንግሥት አከል መኖሪያ ቤት ማሠሪያ እየዋለ ነው። መቀሌ ላይ ህወሃት 40ኛ ልደቱን ለማክበር ወደ ግማሽ ቢልዮን ብር ባወጣ ማግስት በአማራ ስም ለወያኔ ባርነት የገባው ብአዴን 300 ሚሊዮን ወጪ በማድረግ በረሃብተኛው ሕዝብ አናት ላይ እየጨፈረ ነው:: ይህ የኢትዮጵያን ሕዝብ መናቅ ብቻ ሳይሆን ደግሞ ደጋግሞ ከመግደል የሚቆጠር ወንጀል ነው።
ለመሆኑ የአየር ንብረት መዛባት እየተደጋገመ ለሚመጣ ችጋርና ቸነፈር በቂ ምክንያት ሆኖ ያውቃልን? ለምንድነው ፍትህና ነፃነት በሰፈነባቸው አገሮች ውስጥ ዝናብ ጠፍቶ የእርሻ ምርት ቢቀንስ እንኳን ሰው በረሀብ የማይሞተው? አስከፊ የረሀብ ዜናዎች የሚሰማባቸው አገሮች በሙሉ ነፃነት የታፈነባቸው አገሮች መሆናቸውስ የአጋጣሚ ጉዳይ ነው? ለምንድነው ተደጋግሞ ከሚመጣ የረሀብ አዙሪት መውጣት ያቃተን?
የእነዚህ ሁሉ ጥያቄዎች መልስ አጭርና ቀጥተኛ ነው። ለችግሮች መፍትሄ መሻት የሚቻለው በነፃነት ማሰብ የሚችል ጭንቅላት ሲኖር ነው። በባርነት ጨለማ ውስጥ ያለ ጭንቅላት ለችግሮች መፍትሄ የማፍለቅ አቅም የለውም። እንዲያውም እንዲህ ዓይነቱ ድኩም ጭንቅላት ችግሮችን ማሸነፍ ሳይሆን ተሸናፊነትን ተቀብሎ ከችግሮች ጋር ተስማምቶና ተወዳጅቶ መኖርን ይመርጣል። ለዚህም ነው የአስተዳደር በደልና ረሀብ ምክንያትና ውጤት ብቻ ሳይሆን እጅና ጓንትም ጭምር የሆኑት።
ነፃነት ያለው ሕዝብ ረሀብን እንደሚያሸነፍ ተደጋግሞ የታየ ጉዳይ ነው። ለዚህም ነው ረሀብን የተፈጥሮ ሚዛን መዛባት ውጤት ብቻ አድርጎ ማቅረብ እውነትን መሸፈጥ የሚሆነው። ረሀብ የብልሹ አስተዳደር ውጤት መሆኑ ያፈጠጠ፣ ያገጠጠ ሀቅ ነው። ከረሀብ መገላገያ መንገድም የተበላሸ አስተዳደር ተወግዶ ኃላፊነት የሚሰማው፣ የዜጎች የማሰብ ነፃነት የሚያረጋግጥ ሕዝባዊ አስተዳደር ሲኖር ነው።
አገራችን ኢትዮጵያን የረሀብ ቀጠና ካደረጉ የ24 ዓመታት የወያኔ “የዘርፈህ ብላ” የኢኮኖሚ ፓሊሲ ውጤቶች መካከል አንዳንዱን ለአብነት ያህል መዘርዘር ይቻላል።
1.ገበሬና መሬት ተለያይተዋል። ኢትዮጵያዊያን አርሶ አደሮች መሬት አልባ ሆነዋል። ለም መሬቶች በኢንቨስትመንት ስም ለህወሓት ጉልተኞችና ምስለኔዎቻቸው ታድሏል፤ እነሱ ደግሞ በተራቸው ለባዕዳን ሽጠውታል። ኢትዮጵያዊው አርሶ አደር በሀገሩ ጭሰኝነት እንኳን አጥቶ ለቀን ሠራተኝነትና ልመና ተዳርጓል። በዚህም ምክንያት ገበሬው እንኳንስ ትልቁን የአየር መዛባት ትንሿንም የዋጋ ንረት መቋቋም እስከማይችልበት ደረጃ ተዳክሟል።
2.ዘርን መሠረተ ባደረገ ክልላዊ ድንበር ሳቢያ ኢትዮጵያዊው ጎበዝ አርሶ አደር አንዱ ቦታ ቢከፋ ወደ ተሻለ ቦታ ተዛውሮ ማረስ አልቻለም። ከሰሜን ወደ ደቡብ ከሄደ የአገራችን አርሶ አደር ይልቅ ባህር ተሻግሮ የመጣ ኤንቨርስተር ነኝ ባይ መሬት ማግኘት ይቀለዋል። እንዲያውም ኢትዮጵያዊው ገበሬ በዱላና በጥይት ሲባረር፤ ከባዕድ አገር የመጣው ብድርና ማበረታቻዎች ይሰጠዋል።
3.የህወሓት ባላሥልጣኖችና በየቦታው ያስቀመጧቸው ምስለኔዎቻቸው ራሳቸውን ባለሚሊዮኖች፣ ከፍ ሲልም ባለ ቢሊዮኖች አድርገዋል። እነዚህ በአንድ ጀምበር ከትቢያ የተነሱ ቱጃሮች ከገንዘብ በተጨማሪም የጄኔራልነት፣ የሚኒስቴርነት፣ የክልል ገዢነት፣ እጅግ ቢያንስ የቢሮ ኃላፊነት ሥልጣንን ኪሳቸው ውሰጥ ከተዋል። የመንግሥት ሥልጣንና ሃብት ይኸን ያህል የተቆራኙበት ሥርዓት በኢትዮጵያ ኖሮ አያውቅም። የጥቂቶች ያለአገባብና ያለቅጥ መክበር በአንፃሩ ደግሞ የብሃኑን ሕዝብ መደህየት ረሀብ እጣ ፈንታችን እንዲሆን አድርጓል።
4.በአቋራጭና በፍጥነት ለመክበር አስተማማኙ መንገድ የገዛ ራስ ጥረትና ታታሪነት ሳይሆን ቅጥፈት፣ አጭበርባሪነትና ሎሌነት ማደር መሆኑን የህወሓት አበጋዞች በተግባር እያሳዩ ሠርቶ፣ ለፍቶ ማደግ ሞኝነት እንዲሆን አድርገውታል። በዚህም ምክንያት በባህላችን ውስጥ ኮትኩተው ያሳደጓቸው አድርባይነት፣ ስንፍናና እና ልመና ችግርን የመጋፈጥ አቅማችንን ሰልበውታል።
5.ደኖቻችን ተጨፍጭፈው፣ ለም መሬታችን ተሸርሽሮ በማለቁ የግብርናችን ምርታማነት በእጅጉ ቀንሷል። በህወሓት የአገዛዝ ዘመን የደን ጭፍጨፋና የመሬት መሸርሸር በአስደንጋጭ ሁኔታ ጨምሯል። አገሪቷ በፍጥነት ወደ ምድረበዳነት እየተቀየረች ነው።
6.ኢትዮጵያዊያን ገበሬዎች ድርቅን መቋቋም ስለሚችሉ ሰብሎች ወይም የአስተራረስ ዘዴዎች ማሰብ፣ መመራመርና መፈተሽ አይችሉም። አዲስ ነገር መሞከር “የኢህአዴግ የግብርና ፓሊሲን“ በመቃወም ወንጀል የሚያስቀጣ ተግባር ሆኗል። በዚህም ምክንያት ገበሬው ድርቅን መቋቋሚያ አዳዲስ ዘዴዎች መፈለግ ቀርቶ በተለምዶ የሚያውቃቸውንም መጠቀም አልቻለም።
7.የህወሓት አገዛዝ፣ እንደ ኢኮኖሚው ሁሉ የኢትዮጵያን ሕዝብ ብዛት ሊቆጣጠር የሚሞክረው ቢሮ ውስጥ ቁጭ ተብሎ በሚደረግ የቁጥር ጨዋታ ነው። አገዛዙ ውጤታማ የስነ ሕዝብ ፓሊሲ የለውም፤ እንኳንስ የቀጣይ ዓመታት የሕዝብ እድገት ምጣኔን ሊቆጣጠር አሁን ያለነው ቁጥራችን ስንት እንደሆነ እንኳን በትክክል ሊነግረን አልቻለም፤ ረሀብ ነው መብዛታችንን እየነገረን ያለው።
አርበኞች ግንቦት 7፡ የአንድነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ እነዚህና የመሳሰሉት ጭብጦችን በማንሳት የረሀቡ መሠረታዊ ምክንያት የህወሓት አገዛዝ ያሰፈነው ብልሹ አስተዳደር መሆኑን በአንጽዖት ይናገራል። ሕዝባችን በነፃነት ማሰብ፣ መመራመር፣ መፈተሽ ቢችል ኖሮ ረሀብን መከላከያ ብልሃት ማግኘት ባላቃተውም ነበር ብሎ አርበኞች ግንቦት 7 ያምናል። ረሀብን ለማጥፋት ህወሓትን ከሥልጣን ማስወገድ ከምንጊዜውም በላይ ወሳኝ የሆነ ጊዜ ላይ ተደርሶአል ብሎ አርበኖች ግንቦት 7 ያምናል።
ነገር ግን ረሀብ ጊዜ አይሰጥም። የፓለቲካ ሥርዓት ለውጥ በሞት አፋፍ ላይ ላለ ወገናችን መፍትሄ አይሆንም። ስለሆነም ለረሀቡ መሠረታዊ መፍትሄ የሆነውን ትግላችንን ሳንዘነጋ የወገኖቻችንን ሕይወት ለመታገድ የምንችለውን ሁሉ እንድናደርግ አርበኞች ግንቦት 7 ጥሪ ያደርጋል። ሲቪክ ማኅበራት የተራበው ወገናችን የወያኔ መጠቀሚያ ሳይሆን የአስቸኳይ ጊዜ እርዳታ የሚያገኝበት መንገድ እንዲያፈላልጉ እና ወገን ለወገን የሚቆምበትን ዘመቻ እንዲያስተባብሩ ጥሪ ያደርጋል። ለወገኖቻችን የሚላከው እርዳታ ከዚህ በፊት እንደነበረው ሁሉ ወደአገዛዙ ባለሥልጣኖች የግል ኪስ እንዳይፈስ ጥንቃቄ እንዲደረግ ያሳስባል። ለወገኖቻችን ለመድረስ እያንዳንዳችን በግል፤ እንዲሁም በቡድን የተቻለንን ሁሉ እናድርግ።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!
ኅዳር 3 ቀን 2008 ዓ.ም.

Sunday, November 15, 2015

ጋዜጠኞችና የረድኤት ድርጅቶች ረሃቡ ወደተከሰተበት ቦታ እንዳይሄዱ ተከለከለ * መንግስት ረሃቡን ለመደበቅ ከፍተኛ መመሪያ አስተላለፈ -

ሕወሓት የሚመራው የኢትዮጵያ ገዢ በኢትዮጵያ የተከሰተውን እና 15 ሚሊዮን ሕዝብን ለረሃብ ያጋለጠውን አደጋ ለመሸፋፈን ከፍተኛ የሆነ የፕሮፓጋዳ ሥራዎችን ከመስራት በተጨማሪ መረጃዎች እንዳይወጡ እስከማፈን ደረጃ መድረሱን ምንጮች ለዘ-ሐበሻ አስታውቀዋል::
ፎቶ ፋይል
ፎቶ ፋይል
የውጭ ጉዳይ ሚኒስተር መስሪያ ቤት; የመንግስት ኮምዩኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስተርና የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽሕፈት ቤት በአንድ ላይ ተቀናጅተው እየሰሩት የሚገኘው የመረጃዎችን የማፈን ሥራ ታች ድረስ ወርዶ እስከ ፓርቲ አባላትና “ደጋፊ” የተባሉ ሰዎች ጭምር እንዲሰራበት እየተደረገ ነው:: “ረሃቡን አስታከው ለውጭ መንግስታት ሊያሳጡን የሚሞክሩትን መታገል አለብን” በሚል እነዚህ ሶስት መስሪያ ቤቶች ባወጡት መመሪያ መሠረት የውጭ ጋዜጠኞችም ሆነ የረድኤት ድርጅቶች ረሃቡ ወዳለበት ቦታ ሄደው ፎቶ እንዳያነሱ; ቭዲዮ እንዳይቀርጹ; ማንኛውንም ቃለምልልስ እንዳያደረጉ ተከልክሏል:: በተለይ ቢቢሲ በቅርቡ በኢትዮጵያ በአንድ ትንሽ ክልል ስፍራ ብቻ በቀን 2 ህፃናት በረሃቡ እየሞቱ እንደሆነ መዘገቡን ተከትሎ አለም አቀፍ ሚዲያዎች እና የአፍቃሬ ሕወሓት መንግስት ደጋፊ የሆኑ ሃገራት ሳይቀር ከዚህ ቀደም “ልማታዊ መንግስት” እያሉ ሲያሞካሹ የነበረውን አፋቸውን በመጠራረግ ረሃቡን እና መንግስት የሚከተለውን ፖሊሲ እንደገና እየመረመሩ እንደሚገኙ ዲፕሎማቲክ ምንጮች ይናገራሉ::
እንደ ዘ-ሐበሻ ምንጮች ዘገባ በቅርቡ በቢቢሲ የቀረበችውን እናት የአማራ ክልል ጋዜጠኞች አስገድደው ቃለምልልስ ያደረጓት ሲሆን በቅርቡም በመንግስት ሚዲያዎች ላይ “አልራበኝም” ዓይነት ንግግር በማስደረግ የቢቢሲን ዘገባ ለማስተባበል ሥራ እየተሰራ ይገኛል::
ከሥስቱ መስሪያ ቤቶች በተላለፈው መመሪያ መሠረት የመንግስት ሃላፊዎች ከላይ እስከታች በየሶሻል ሚዲያው በመውጣት ችግሩን መንግስት ተቆጣጥሮታል እያሉ መጻፍ እና መናገር አለባቸው:: “ተቃዋሚዎች የመንግስታችንን መልካም ገጽታ ለማጠልሸት ሆን ብለው የሚያደርጉት ሤራ ነው” እያሉም በውጭ ያሉ ኤምባሲዎችና ተላላኪዎች እንዲያነገሩ ትዕዛዝ ከመተላለፉም በላይ መንግስትን ይደግፋሉ ለተባሉ የውጭ ጋዜጠኞች ወደ ሃገር ቤት እንዲገቡና መልካሙን ነገር ብቻ እንዲዘግቡ ኢምባሲዎች መሥራት እንዳለባቸውም የወጣው መመሪያ ሲያመለክት ስለመንግስት መጥፎ ነገር ሊናገሩ ይችላሉ የተባሉ ጋዜጠኞች ግን ረሃቡ ወዳለበት ቦታ እንዳይሄዱ/ ምስል መቅረጽና ቃለምልልስ ማድረግ እንዳይችሉ የኮምዩኒኬሽን መስሪያ ቤት ፈቃድ እንዳይሰጥ ት ዕዛዝ ወርዷል::
በስልጣን ላይ ያለው መንግስት 15 ሚሊዮን ሕዝብ በመራቡ የተነሳ በወዳጅ ሃገሮቹ ሳይቀር በመጥፎ አይን እየታየመምጣቱ በስርዓቱ ውስጥ “ገጽታችን ተበላሸ” በሚል ራሱን የቻለ ሽብር ፈጥሯል:: (ዘ-ሐበሻ)
- See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/48271#sthash.STvv23Es.dpuf

Wednesday, November 11, 2015

ለ6 ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ከ150 ሚሊዮን ብር ባላነሰ ገንዘብ የግል መኖሪያ ቤት እየተሰራላቸው ነው፡

ለከፍተኛ የኢህአዴግ ባለሥልጣናት መኖሪያ የሚሆን ለእያንዳንዳቸው 25 ሚሊየን ብር የሚያወጡ፣ 6 ዘመናዊ መኖሪያ ቤቶች በአዲስ አበባ ሲኤምሲ አካባቢ ከፍተኛና ምቹ ቦታ ተመርጦ እየተገነቡላቸው መሆኑን የፌዴራል መንግሥት ቢሮዎች ግንባታ ፕሮጀክት ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ተክለጻድቅ ተክለአረጋይን ለ ሸገር ኤፍ ኤም 102 ተናግረዋል።
የሕንጻ ግንባታ ስራቸው በመጠናቅ ላይ ያሉት እነዚህ ዘመናዊ መኖሪያ ቤቶች ከመሬት በታች አንድ ከመሬት በላይ ባለ ሁለት ፎቅ ሲሆኑ የመዋኛ ገንዳዎችን ጨምሮ የተለያዩ ዲዛይኖችን ( ቅርጻቅርጾችን) የሚያሟሉ አጠቃላይ ወጪያቸው ከ154 ሚሊዮን ብር በላይ እንደሚሆን ተናግረዋል። እነዚህ መኖሪያ ቤቶች የጡረተኛ ባለስልጣናቱ ዘላለማዊ የግል ንብረት ሆነው ያገለግላሉ ሲሉ ባለስልጣኑ ተናግረዋል።
ቀጣይ ሁለተኛ ዙር ምቹ የባለስልጣናት መንደር ግንባታም እንዲሁ በመንግስት ወጪ ይጀምራል። በትግራይ መቀሌ ለህወሃት ከፍተኛ ባለስልጣናት የተሰሩ መኖሪያ ቤቶች ሰፈር አፓርታይድ በመባል ይጠራል። የቀድሞው ፕሬዚዳንት ግርማ ወልደጊዮርጊስ ለሚኖሩበት ቤት መንግስት በወር 400 ሺህ ብር የቤት ኪራይ ወጪ ከታክስ ከፋዩ ሕዝብ እየወሰደ ይከፍላል።
ኢትዮጵያ 15 ሚሊዮን የሚጠጉ ዜጓቿ አሁንም በከፍተኛ ረሃብ እየተሰቃዩ ናቸው። ከግማሽ በላይ የሚሆነው ህዝብ ከአንድ ዶላር በታች ወይም ከ1 ዶላር እስከ 2 ዶላር ባለ የቀን ገቢ ይተዳደራል። አገሪቱ ከ30 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር ወይም ከ1 ትሪሊዮን 200 ቢሊዮን ብር በላይ ብድር ወይም እዳ አለባት።
ምንጭ ፤- ኢሳት

ሰማያዊ ፓርቲ ህዳር 18 ህዝባዊ ስብሰባ ጠራ • መስተዳደሩ ለ5ኛ ጊዜ ማሳወቂያ ደብዳቤውን አልቀበልም ብሏል • ‹‹መልካም አስተዳደር የሚባለው ከወሬ ያለፈ እንዳልሆነ ያሳያል›› ኢ/ር ይልቃል ጌትነት -

ሰማያዊ ፓርቲ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ከአባላቱና ደጋፊዎቹ ጋር ውይይት ለማድረግ ህዳር 18/2008 ዓ.ም በመብራት ኃይል አዳራሽ ህዝባዊ ሰብሰባ እንደሚያደርግ ሊቀመንበሩ ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡ ይሁንና የማሳወቂያ ደብዳቤውን ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ፅ/ቤት በአካል ለማድረስ ጥረት ቢደረግም በሰራተኞቹ ዘንድ ለአምስተኛ ጊዜ ‹‹ኃላፊዎቹ የሉም፡፡ እኛ አንቀበልም›› መባላቸውን ም/ሊቀመንበሩ አቶ ነገሰ ተፋረደኝ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡ ‹‹ጠዋት ስንሄድ፣ ከሰዓት ኑ፣ ከሰዓት ስንሄድ፣ ስብሰባ ላይ ናቸው ጠዋት ኑ እያሉ 5 ጊዜ አንቀበልም ብለውናል፡፡›› ሲሉ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡ ‹‹ለአንድ መስሪያ ቤት ደብዳቤ ለማድረስ በመዝገብ ቤት አሊያም በፀኃፊ በኩል መቀበል በቂ ነው፡፡ ኃላፊውን የግድ መጠበቅ አያስፈልግም ነበር፡፡›› ያሉት ኢ/ር ይልቃል ‹‹ይህ አስተዳደራዊ በሆነ መንገድ ህገ መንግስታዊ መብትን የሚያግዱበት ስልት ነው›› ብለዋል፡፡ ሊቀመንበሩ አክለውም ‹‹ስለመልካም አስተዳደር በሚያወሩበት በአሁኑ ወቅት አስተዳደራዊ በሆነ መንገድ መብትን እያገዱ መቀጠላቸው መልካም አስተዳደር የሚባለው ከወሬ ያለፈ እንዳልሆነ የሚያሳይ ነው›› ብለዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ፅ/ቤት ለ5ኛ ጊዜ የሰማያዊ ፓርቲን የስብሰባ ማሳወቂያ ደብዳቤ በአካል መቀበል ባለመፈለጉ ፓርቲው ደብዳቤውን በሪኮመንዴ ለመላክ መገደዱን ፓርቲው ለፅ/ቤቱ በላከው ደብዳቤ ላይ አመላክቷል፡፡ በዚህም መሰረት ዛሬ ህዳር 1/2008 ዓ.ም ፓርቲው ማሳወቂያውን ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ፅ/ቤት በሪኮመንዴ መላኩን ሊቀመንበሩ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡ - See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/48184#sthash.cioSnkrv.dpuf

Tuesday, November 10, 2015

በሰሜን ጎንደር ዞን በርካታ የልዩ ሃየል አባላትና ሰላማዊ ዜጎች ተገደሉ

ኢሳት ዜና :-ከቅማንት ብሄረሰብ ጥያቄ ጋር በተያያዘ በአርሶ አደሩና በክልሉ ልዩ ሃይል መካከል ከማውራ 15 ኪሜ ርቃ በምትገኘዋ ሮቢት አካባቢ እንዲሁም በላይ አርማጭሆ ዋና ከተማ ትክል ድንጋይ ከፍተኛ ውጥረት ነግሶአል። እስከትናንት ድረስ በአርሰዶ አደሩና በልዩ ሃይል መካከል በተደረገ የተኩስ ለውጥጥ ከ100 በላይ የልዩ ሃይል አባላት ሲገደሉ፣ ከ36 ያላነሱ ንጹሃን ዜጎች ደግሞ በልዩ ሃይል አባላት ተገድለዋል። ዛሬ በበርካታ መኪኖች የተጫኑ የመከላከያ ሰራዊት አባላትና የልዩ ሃይል አባላት ከባድ መሳሪያዎችን ሳይቀር ወደ ትክል ድንጋይ በማስገባቱ ህዝቡ ቤቶቹን ዘግቶ ከመቀመጡም በላይ፣ ትምህርት ቤቶች የመንግስት መስሪያ ቤቶችና የንግድ ድርጅቶች በሙሉ ተዘግተዋል። የልዩ ሃይል አባላት የተገደሉባቸውን ባልደረቦቻቸውንሊበቀሉ ነው በሚል የቻለው ወደ ጫካ መውጣቱንም ያካባቢው ነዋሪዎች ለኢሳት ተናግረዋል። በርካታ የተገዱ የልዩ ሃይል አባላት በአዘዞ የመከላከያ ካምፕ እና በጎንደር ሪፈራል ሆስፒታል መወሰዳቸውን የሚደርሱን መረጃዎች ያመለክታሉ። የልዩ ሃይል አባላት እህትማማች ሴቶችን በጩቤ ገድለው መገኘታቸውን የሚናገሩት የአካባቢው ነዋሪዎች፣ አስነዋሪ በሆነ መልኩ ባለትዳር ሴቶችን ሳይቀር መድፈራቸው የህዝቡን ቁጣ አባብሶታል በማለት ነዋሪዎች ተናግረዋል። ጥያቄውን ከሚያስተባብሩ ወገኖች መካከል አንድ ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ ሰው ለኢሳት እንደተናገሩት በህዝቡ በኩል ከልዩ ሃይል አባላት መካከል 102 ከህዝቡ ደግሞ 33 ሰዎች ተገድለዋል ይላሉ።

Monday, November 9, 2015

በጎንደር ጭልጋና ትክል ድንጋይ መካከል በሚገኝ ማውራ የተባለ ቦታ በገበሬዎችና በህወሓት ልዩ ኃይል ጦር መካከል ውጊያ ተካሄደ - See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/48081#sthash.FOzLOtJp.dpuf

በጎንደር ጭልጋና ትክል ድንጋይ መካከል በሚገኝ ማውራ የተባለ ቦታ ላይ በአካባቢው ገበሬዎችና በህወሓት ልዩ ኃይል ጦር መካከል ከፍተኛ ግጭት ተቀስቅሶ ከባድ ውጊያ እየተካሄደ ይገኛል፡፡
ፍልሚያው የተጀመረው ትናንት ረፋድ ላይ ሲሆን አሁንም ተባብሶ እንደቀጠለ ነው፡፡ አካባቢው ትንሽ እንኳን ፋታ በሌለው ተከታታይ የጦር መሳሪያ ፍንዳታ ድምፅ እየተናጠ ይገኛል፡፡
እስካሁን ድረስ በደረሰን መረጃ መሰረት በትንሹ 5 የልዩ ኃይሉ ጦር አባላት ተገድለዋል ከ9 በላይ ደግሞ ቆስለዋል፡፡ ነገር ግን በማውራ ገበሬዎች በኩል የደረሰ ጉዳት ይኑር አይኑር ምንም የታወቀ ነገር የለም፡፡
የጎንደር-ጭልጋ ማውራ ገበሬዎችንና የህወሓትን ልዩ ኃይል ለመዋጋት ያበቃቸው ምክንያት ምን እንደሆነ በውል ተለይቶ አልታወቀም፤ ነገር ግን በጭልጋና አካባቢው ቀደም ሲል የተነሳው የብሄር ጥያቄ ሳይሆን እንዳልቀረ ምንጮቻችን ያላቸውን ግምት አስቀምጠዋል፡፡
በተጨማሪም በጭልጋና አካባቢው የሚገኙ ትምህርት ቤቶች ከግጭቱ አንድ ሳምንት ቀደም ብለው መዘጋታቸውና ሙሉ በሙሉ ማስተማር ማቆማቸው ተገልጿል፡፡
- See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/48081#sthash.FOzLOtJp.dpuf

Monday, November 2, 2015

የአዲስ አበባና አካባቢዋ ወተት ከፍተኛ መርዛማ ህፃናትን የሚያቀጭጭ እና የሚያሳጥር ኬሚካል አለው ተባለ -

ነገሩ፣ ለዘመናት ከምናውቀው እውቀት የተለየ በመሆኑ ግራ ማጋባቱ አይቀርም፡፡ እስካሁን ለሕፃናት ዕድገትና ጥንካሬ ጥሩ ነው በማለት ሕፃናትን ስንመግብ የኖርነው ወተት፤ በተቃራኒው ለሕፃናት ዕድገት ጥሩ አይደለም፤ ያቀጭጫቸዋል ቢባሉ ምን ይላሉ? የሚገርም ነው!ሰሞኑን በሂልተን ሆቴል ሲካሄድ በቆየው 4ኛ የአፍሪካ የምግብና የኑትሪሽን ፎረም ላይ አንድ ተመራማሪ፤ በመርዛማ ኬሚካሎች (አልፋ ቶክሲን) ላይ ያደረጉትን የምርምር ውጤት ሲያቀርቡ፤ እግረ መንገዳቸውን የአዲስ አበባና አካባቢዋ ወተት ከመጠን በላይ መርዛማ ኬሚካል (አልፋ ቶክሲን) እንዳለው ገልፀዋል፡፡ ተመራማሪው ዶ/ር አሻግረ ዘውዱ፤ ዓለም አቀፉ የእንስሳት ምርምር ኢንስቲትዩት (ILRI) ባወጣው ሪፖርት፤ በ2016 በአዲስ አበባና አካባቢዋ ባደረገው ጥናት፣ ከተሰበሰቡት 140 ናሙና ከ90 በመቶ በላይ ዓለምአቀፍ ሕግ ከሚፈቅደው በላይ መርዛማ ኬሚካል (አፍላቶክሲን M1) እንዳለው ማስታወቁን ተናግረዋል፡፡ አልፋ ቶክሲን በሻጋታ ምክንያት የሚፈጠር መርዛማ ኬሚካል ነው ያሉት ተመራማሪው፤ መርዛማ ኬሚካሉ ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍሎች ቢጐዳም በሕፃናት ላይ የበለጠ ጉዳት ያደርሳል፣ መቀጨጭና መጫጫት ያስከትላል፡፡ በዕድሜያቸው ልክ ቁመታቸው አያድግም፡፡ በኢትዮጵያ 40 በመቶ ሕፃናት ቀጫጫ ናቸው፡፡ መርዛማ ኬሚካሉ ከማጫጨት በተጨማሪ ረዥም ዕድሜ ሲቆይ የጉበት ካንሰር ያስከትላል ብለዋል፡፡ አልፋ ቶክሲኖች የተለያዩ ናቸው፡፡ እህል ላይ የሚገኙትና በይበልጥ የሚታወቁት 4 ናቸው፡፡ እነሱም B1 B2 G1 G2 ይባላሉ ያሉት ዶ/ር አሻግሬ፤ እህሉ ላይ የሚገኘውን B1 አልፋ ቶክሲን የበላ ከብት በሰውነቱ ውስጥ በሚካሄደው ሜታቦሊዝም፣ B1 መርዛማ ኬሚካል ወደ M1 ይቀየራል፡፡ ኤች አይ ቪ ከእናት ወደ ልጅ እንደምታስተላልፍ እናት ለልጇ ጡት ስታጠባ መርዛማውን ኬሚካል ወደ ሕፃኑ ታስተላልፋለች፡፡ ከብትም እንደዚሁ፡፡ ሕፃኑ በአልፋ ቶክሲን የሚጠቃው፣ ጡት መጥባት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ ነው በማለት አስረድተዋል፡፡ ወተት ለሕፃናት ዕድገት ጥንካሬና ውፍረት ጥሩ ነው ስለሚባል ወተት እየጠጡ ያድጋሉ፤ ለአልፋ ቶክሲን እየተጋለጡ ናቸው ያሉት ተመራማሪው፤ “በወሎ ድርቅ ጊዜ የእርጐ ፈንገስ የሚባል ነገር ተፈጥሮ ነበር፡፡ የሚበላ ነገር ሲጠፋ ፈንገስ የተቀላቀለበት ምግብ በልተው፤ ጋንግሪን ተፈጥሮባቸው እግራቸው የተቆረጠ ብዙ ሰዎች ነበሩ፡፡” ብለዋል፡፡ ዓለምአቀፉ የእንስሳት ምርምር ኢንስቲትዩት ያወጣውን መረጃ በተመለከተ፤ መንግስት ከኢትዮጵያ ፐብሊክ ኢንስቲትዩት፣ የደረጃዎች ምዘናና ተስማሚነት፣ የምግብ ሳይንስና ኑትሪሽን ማዕከል እንዲሁም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የተውጣጡ ባለሙያዎች ጥናት እንዲያደርጉበት ኮሚቴ አቋቁሟል፡፡ ውጤቱ ልክ እንደተባለው ከሆነ ምን እናድርግ? በማለት ምክክር ይደረጋል ያሉት ዶ/ር አሻግሬ፤ ልክ ካልሆነ ደግሞ ኅብረተሰቡ ትክክለኛ መረጃ እንዲያገኝ ይደረጋል ብለዋል::   ምንጭ አዲስ አድማስ ጋዜጣ (ዛሬ በአዲስ አበባ ታትሞ የወጣ) - See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/47909#sthash.9lxCGAJc.dpuf